ኢፒኦ ሳምንታዊ: ሐምሌ 8-14, 2015
Reports on political conflicts in Ethiopia from Hamele 8 to 14, 2015, highlighting key statistics and events.
Also available in English
- የፖለቲካ ግጭት ኩነቶች ብዛት: 1,058
- በፖለቲካ ግጭቶች ምክንያት ሪፖርት የተደረጉ የሟቾች ቁጥር: 4,471
- በሰላማዊ ሰዎች ላይ በተሰነዘሩ ጥቃቶች ምክንያት ሪፖርት የተደረጉ የሟቾች ቁጥር: 1,940
- የፖለቲካ ግጭት ኩነቶች ብዛት: 11
- በፖለቲካ ግጭቶች ምክንያት ሪፖርት የተደረጉ የሟቾች ቁጥር: 84
- በሰላማዊ ሰዎች ላይ በተሰነዘሩ ጥቃቶች ምክንያት ሪፖርት የተደረጉ የሟቾች ቁጥር: 6
ኢትዮጵያን በተመለከተ በቁጥር የተደገፉ መረጃዎችን ከኢፒኦ የመረጃ መዝገብ እንዲሁም በዋናው የአክሌድ ኤክስፖርት መሳሪያ ውስጥ ማግኘት ይችላሉ።

የሁኔታዎች አጭር መግለጫ
ባለፈው ሳምንት በጋምቤላ ክልል የብሔር ታጣቂዎች የተሳተፉበት ጠንከር ያለ ግጭት የተከሰተ ሲሆን በአማራ ክልል በአካባቢው ባለስልጣናት ላይ ያነጣጠረ ግድያ ቀጥሏል። በኦሮሚያ ክልል ባለፈው ሳምንት አንድ አለመረጋጋት ክስተት – አመጽ የተቀላቀለበት ሰልፍ – የተመዘገበ ሲሆን ይህም በክልሉ ይታይ የነበረው አለመረጋጋት መቀነሱን አሳይቷል።
በጋምቤላ ክልል ግጭት የተቀሰቀሰ ሲሆን በአኙዋክ እና በኑዌር ብሔረሰብ ታጣቂዎች መካከል ተደጋጋሚ ውጊያዎች በኢታንግ ልዩ ወረዳ እንዲሁም በጋምቤላ ከተማ ተዘግበዋል (ከዚህ በታች ያለውን ካርታ ይመልከቱ)። እንደ አክሌድ ዳታ ከሆነ በባለፈው ሳምንት ውጊያዎች ምክንያት ቢያንስ 70 ሰዎች መሞታቸውን ሪፖርት ተደርጓል። የበለጠ ዝርዝር መረጃ ሲገኝ የሟቾች ቁጥር ሊጨምር ይችላል። የጋምቤላ ክልል ግጭቱን ለማስቆም ሐምሌ 11 ቀን የምሽት ሰዓት እላፊ አውጇል። የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ኮሚሽን እንደዘገበው ከሆነ ከአኙዋክ እና ኑዌር ብሔረሰብ ታጣቂዎች በተጨማሪ በአሁኑ ጊዜ በስደተኞች መጠለያ ካምፖች ውስጥ የሚገኙ ከደቡብ ሱዳን የመጡ ታጣቂዎችም በግጭቱ ሳይሳተፉ አልቀረም።2 በተጨማሪም ሐምሌ 11 ቀን ከደቡብ ሱዳን የመጡ የሙርሌ ብሔር ታጣቂዎች ድንበር ጥሰው በጋምቤላ ከተማ አቅራቢያ በምትገኘው አቦሌ ወረዳ 12 ሰላማዊ ሰዎች ገድለዋል።3

በአማራ ክልል በፀጥታ ኃይሎች እና በፋኖ ታጣቂዎች መካከል የሚደረገው ውጊያ የቀጠለ ሲሆን በማዕከላዊ ጎንደር ዞን በጎንደር ዙሪያ ወረዳ ማክሰኝት ከተማ እና በሰሜን ሸዋ ዞን መርሀቤቴ ወረዳ አለም ከተማ ውጊያዎች ተመዝግበዋል4 (በአማራ ክልል ስላለው የፖለቲካ ግጭት የበለጠ መረጃ ለማግኘት የኢፒኦ ወርሃዊ፡ ግንቦት 24- ሰኔ 23, 2015ን ይመልከቱ)። በተጨማሪም ማንነታቸው ያልታወቁ ታጣቂዎች በጎንደር ከተማ ሐምሌ 12 ቀን አንድ የአካባቢውን ባለስልጣን ተኩሰው ገድለዋል።
በቤንሻንጉል/ጉሙዝ ክልል ቀደም ሲል ትጥቅ ለመፍታት ተስማምተው የነበሩ የጉሙዝ ሕዝብ ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ (ጉሕዴን) አባላት ሃሳባቸውን ቀይረው ግልገልበለስ የሚገኘውን የትጥቅ ማስፈቻ ጣቢያን ለቀው ወተዋል።5 በዚህ እርምጃ ግጭት ዳግም እንዳይቀሰቀስ በመፍራት በቡለን ወረዳ በጉንጂ እና በጎንጎ ቀበሌዎች የሚገኙ በሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎች አካባቢያቸውን ለቀው መፈናቀላቸው ተነግሯል።6 በ2014 ዓ.ም. አጋማሽ ላይ የሰላም ስምምነት ተደርጎ የጉሕዴን ታጣቂዎች እጃቸውን እስኪሰጡ ድረስ የቤንሻንጉል/ጉሙዝ ክልል በተለይም የመተከል ዞን በ2012 እና 2013 በሀገሪቱ ውስጥ ከፍተኛ ግጭት ከሚከሰትባቸው አካባቢዎች አንዱ ነበር (በቤንሻንጉል/ጉሙዝ ክልል ውስጥ ስለተካሄደው የሰላም ሂደት የበለጠ መረጃ ለማግኘት የኢፒኦ ሳምንታዊ: ከመጋቢት 1 – 8፣ 2015ን እና የኢፒኦ ከየካቲት 22 እስከ መጋቢት 22, 2015 ወርሃዊን ይመልከቱ)። የክልሉ ፕሬዝዳንት እንዳሉት ከሆነ ከ5,800 በላይ የቀድሞ ተዋጊዎች በመንግስት የተሃድሶ መርሃ ግብር ውስጥ ተሳትፈዋል።7 ይሁን እንጂ እነዚህ ተዋጊዎች ከአንድ ወይም ከተለያዩ ታጣቂ ቡድኖች እንደነበሩ ግልጽ አይደለም።
ባለፈው ሳምንት በደቡብ ብሔር ብሔረሰቦችና ህዝቦች ክልል በጉራጌ ዞን የመስቃን እና የማረቆ ብሔረሰቦች ላይ ያነጣጠረ ጥቃት መከሰቱ ተዘግቧል። ሐምሌ 12 ቀን በምስራቅ መስቃን ወረዳ በእንሴኖ ከተማ በጋሮሬ እና በንግድ ባንክ 01 ቀበሌዎች ማንነቱ ያልታወቀ ታጣቂ ቡድን ሁለት የማረቆ ብሄረሰብ ተማሪዎችን እና ሁለት የመስቃን ተወላጆችን ጨምሮ አራት ሰላማዊ ሰዎችን ገድሏል። ላለፉት ሁለት አስርት አመታት በመስቃን ወረዳ በሚገኙ በዘጠኝ ቀበሌዎች ላይ በሚነሳ የባለቤትነት ጥያቄ ምክንያት በሁለቱ ብሔረሰቦች መካከል አለመግባባት አለ። ከሰኔ ወር መጨረሻ ጀምሮ በምስራቅ መስቃን ወረዳ የሁለቱ ብሔረሰብ ተወላጅ በሆኑ ሰላማዊ ሰዎች ላይ ያነጣጠረ ሌላ ዙር ጥቃት ተነስቷል (ለበለጠ መረጃ ኢፒኦ ሳምንታዊ: ከሰኔ 24-30, 2015ን ይመልከቱ)።
በመጨረሻም በኦሮሚያ ክልል አዲስ በተቋቋመው የምስራቅ ቦረና ዞን ምክንያት በጉጂ ዞን ያለው አለመረጋጋት ባለፈው ሳምንትም ቀጥሏል። ሐምሌ 8 ቀን ወጣት ተቃዋሚዎች በጎራ ዶላ በኪሊዌ አዲሱን የዞን መዋቅር በመቃወም አምስት ተሽከርካሪዎችን በማስቆም አቃጥለዋል (የምስራቅ ቦረና ዞን መቋቋሙን በመቃወም ስለተደረጉ ሰልፎች የበለጠ መረጃ ለማግኘት የኢፒኦ ሳምንታዊ: ከየካቲት 25 – መጋቢት 1, 2015ን፣ የኢፒኦ ሳምንታዊ: ከግንቦት 26-ሰኔ 2, 2015ን እና የኢፒኦ ሳምንታዊ: ከሐምሌ 1-7, 2015ን ይመልከቱ)። ከዚህ በተለየ ባለፈው ሳምንት በክልሉ ሌላ ምንም አይነት አለመረጋጋት አልተመዘገበም።
Footnotes
- 2
- 3
ጌታሁን አስናቀ፣ ‘የጋምቤላ ክልል ዲማ ወረዳ የሙርሌ ታጣቂዎች የሚያደርሱት ጥቃት ከአቅሜ በላይ ነው አለ፣’ አዲስ ማለዳ፤ ሐምሌ 17, 2015
- 4
ጌታሁን አስናቀ፣ ‘በሰሜን ሸዋ ዞን መርሀቤቴ ከተማ በመከላከያ ሠራዊት አባላት ላይ ጥቃት መፈጸሙ ተገለጸ፣’ አዲስ ማለዳ፣ ሐምሌ 16, 2015
- 5
የኢትዮጵያ ሳተላይት ቴሌቪዥን እና ሬዲዮ፣ ‘ኢሳት አማርኛ ዜና ሐምሌ 13, 2015፣’ ሐምሌ 13, 2015
- 6
- 7
ዋዜማ ሬዲዮ፣ ‘ለቸኮለ ማለዳ! ማክሰኞ ሐምሌ 18/2015 ዓ.ም የዋዜማ ዐበይት ዜናዎች፣’ ሐምሌ 18, 2015