ኢፒኦ ሳምንታዊ: ከሚያዚያ 21- ግንቦት 11, 2015
አማርኛ በሳምንት ዘገባ: የፖለቲካ ግጭቶች አዘቅቅም ወጥመዛች በኦሮሚያ እና አማራ ክልሎች ተመዝግቧል።
Also available in English
- የፖለቲካ ግጭት ኩነቶች ብዛት: 1,130
- በፖለቲካ ግጭቶች ምክንያት ሪፖርት የተደረጉ የሟቾች ቁጥር: 5,984
- በሰላማዊ ሰዎች ላይ በተሰነዘሩ ጥቃቶች ምክንያት ሪፖርት የተደረጉ የሟቾች ቁጥር: 2,632
- የፖለቲካ ግጭት ኩነቶች ብዛት: 44
- በፖለቲካ ግጭቶች ምክንያት ሪፖርት የተደረጉ የሟቾች ቁጥር: 89
- በሰላማዊ ሰዎች ላይ በተሰነዘሩ ጥቃቶች ምክንያት ሪፖርት የተደረጉ የሟቾች ቁጥር: 46
ኢትዮጵያን በተመለከተ በቁጥር የተደገፉ መረጃዎችን ከኢፒኦ የመረጃ መዝገብ እንዲሁም በዋናው የአክሌድ ኤክስፖርት መሳሪያ ውስጥ ማግኘት ይችላሉ።

የሁኔታዎች አጭር መግለጫ
ከጥር ወር መጨረሻ ጀምሮ ከነበረው አንጻራዊ መረጋጋት በኋላ ባለፉት ሁለት ሳምንታት ውስጥ በኦሮሚያ ክልል ግጭት እየጨመረ መጥቷል። በአማራ ክልል ሚያዚያ 19 ቀን የአማራ ብልፅግና ፓርቲ ሀላፊ እና የፓርቲው ስራ አስፈፃሚ ኮሚቴ አባል መገደላቸውን ተከትሎ በተለያዩ አካባቢዎች ውጥረት ነግሶ የነበረ ሲሆን በሸዋ ሮቢት፣ ጎንደር፣ ደብረ ሲና፣ ማጀቴ እና አንስጾኪያ ከተሞች ግጭት ተፈጥሮ ነበር (ስለ ግድያው ተጨማሪ መረጃዎችን ለማግኘት ኢፒኦ ሳምንታዊ: ሚያዚያ 14-20, 2015ን ይመልከቱ)።
በኦሮሚያ ክልል የፖለቲካ ግጭት የጨመረው በኦሮሞ ነፃነት ግንባር (ኦነግ)-ሸኔ (የኦሮሞ ነፃነት ጦር በመባልም የሚታወቀው) እና በመንግስት መካከል በታንዛኒያ እየተካሄደ የነበረው የመጀመሪያው ዙር የሰላም ንግግር መጠናቀቁን ተከትሎ ነው። ንግግሩ በሚያዚያ 25 ቀን "ቁልፍ ጉዳዮች" ላይ ባለመግባባት ተጠናቋል።2 ምንም እንኳን ሁለቱም ወገኖች በሁለተኛው ዙር የሰላም ንግግር እንደሚሳተፉ ቢጠቁሙም3 በኦሮሚያ ክልል በኦነግ-ሸኔ እና በኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት መካከል ዳግም ውጊያ መቀስቀሱን የሚገልጹ ሪፖርቶች መውጣት የጀመሩት ሁለቱ ወገኖች በታንዛኒያ እየተካሄደ የነበረው ንግግር እንዳለቀ ሳምንት ባልሞላ ጊዜ ውስጥ ነው። እንደ ኦነግ-ሸኔ ከሆነ የመንግስት ኃይሎች በምዕራብ ሸዋ ዞን ጀልዱ እና በምስራቅ ሸዋ ዞን አዳሚ ቱሉ የኦነግ-ሸኔ ኃይሎችን በማጥቃት ሚያዚያ 30 ቀን ውጊያ ቀስቅሰዋል ብሏል። ቡድኑ በድርድር ጊዜ ውጊያዎችን ለመቀነስ በታንዛኒያ የተደረሰውን “መግባባት” መንግስት ጥሷል በማለት ከሷል።4
የመጀመሪያው ዙር የሰላም ንግግር ካለቀ በኋላ አክሌድ በክልሉ ውስጥ ኦነግ-ሸኔ እና የመንግስት ኃይሎች የተሳተፉበት 18 የውጊያ ኩነቶችን መዝግቧል። ከእነዚህ ኩነቶች ውስጥ ግማሹ የተመዘገቡት በምዕራብ ሸዋ ዞን ነው (ከዚህ በታች ያለውን ካርታ ይመልከቱ)። ግንቦት 9 ቀን በሆሮ ጉዱሩ ወለጋ ዞን ጉዱሩ ወረዳ በኮምቦልቻ ከተማ ኦነግ-ሸኔ ከኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት ጋር በመዋጋት ከተማዋን መቆጣጠሩ ተነግሯል። በቢሾፍቱ ከተማ ድሬ ጂቱ ቀበሌ እና በምስራቅ ሸዋ ዞን ወለንጪቲ ከተማ የሚገኙ ፖሊስ ጣቢያዎችን ኦነግ-ሸኔ ካጠቃ በኃላ ውጊያዎች በእነዚህ አካባቢዎች ተዘግበዋል። በቢሾፍቱ ከተማ ቡድኑ ቢያንስ አራት ፖሊሶችን በመግደል እና አንድ ሌላ ፖሊስ በማቁሰል እስረኞችን ማስፈታትና የጦር መሳሪያ መዝረፍ ችሏል። በወለንጪቲ ከተማ ግን የመንግስት ኃይሎች ጥቃቱን የመከቱ ሲሆን የኦነግ-ሸኔን ስድስት ታጣቂዎች ገድለዋል። በሁለቱ መካከል በነበረው ውጊያ ሁለት ሰላማዊ ሰዎች ተገድለዋል።

በተጨማሪም ባለፉት ሶስት ሳምንታት ውስጥ በኦነግ-ሸኔ፣ በፋኖ ታጣቂዎች እና በመንግስት ኃይሎች – በቀበሌ ታጣቂዎች፣ በኦሮሚያ ክልል ፖሊስ እና በኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት – የተፈጸሙ 14 ሰላማዊ ዜጎችን ኢላማ ያደረጉ የጥቃት ኩነቶች በአክሌድ ተመዝግቧል። በሚያዚያ 28 ቀን የኦነግ-ሸኔ አባላት እንደሆኑ የተጠረጠሩ በአፋር ክልላዊ መንግስት “ሽብርተኞች” የተባሉ5 ታጣቂዎች በገቢ ረሱ ዞን የሓንሩካ ወረዳ የብልፅግና ፓርቲ አደረጃጀት ዘርፍ ኃላፊን፣ ወንድማቸውን፣ ሹፌራቸውን እና ሌሎች አምስት ሹፌሮችን ጨምሮ ስምንት ሰዎችን በወለንጪቲ ከተማ አቅራቢያ ባልታወቀ ቦታ መግደላቸው ተነግሯል።
የመንግስት ኃይሎችም በኦሮሚያ ክልል ከህግ አግባብ ውጪ ግድያ ፈጽመዋል በሚል የተከሰሱ ሲሆን ይህ ሪፖርት በሚሸፍነው ጊዜ ውስጥ ሰባት ሰዎችን ገድለዋል ተብሏል። ሁሉም ተጎጂዎች ከኦነግ-ሸኔ ተዋጊዎች ጋር ተባብረዋል ተብለው ተከሰው ነበር። በግንቦት 4 ቀን በተከሰተ አንድ ክስተት አዲስ በተመሠረተው በሸገር ከተማ በሰበታ ከተማ ደረቶ አካባቢ በሚገኝ ባልተጠናቀቀ ህንጻ በጊዜያዊነት በተጠለሉበት ቤት ውስጥ የቀበሌ ታጣቂ እንደሆነ የተገመተ የመንግስት የፀጥታ ኃይል አባል አንድ ግለሰብን፣ ነፍሰ ጡር ሚስቱን እና ጎረቤታቸውን በጥይት ተኩሶ በመግደል የጎረቤታቸውን የሁለት አመት ልጅ እና ባለቤቷን አቁስሏል። ከአንድ ቀን በፊት የተጎጂዎቹ ቤት በኦሮሚያ ክልል መንግስት ግብረ ኃይል ፈርሶ የነበረ ሲሆን የፀጥታ ኃይሎች የተጎጂዎቹ ንብረት ለማዘዋወር ለማገዝ በመጡ ቁጥራቸው ባልታወቁ ቤተሰቦቻቸው ላይ ድብደባ ፈጽመው ነበር። ከእነዚህ ጥቃቶች በስተጀርባ ያለው ምክንያት አልታወቅም።
በአማራ ክልል የአማራ ብልፅግና ፓርቲ ሀላፊ እና የድርጅቱ ስራ አስፈፃሚ ኮሚቴ አባል መገደላቸውን ተከትሎ ባለስልጣናት “ጽንፈኛ ኃይሎችን” ለማስወገድ ቃል ገብተዋል። በዚህም መሰረት በኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት እና በምስራቅ አማራ ፋኖ ታጣቂዎች መካከል በተለያዩ የክልሉ አካባቢዎች ውጊያዎች መከሰታቸው ታውቋል። በባህላዊ የግጭት አፈታት ዘዴዎች ለመሸምገል ሙከራ ቢደረግም የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊ “በጽንፈኛ ኃይሎች” ላይ እርምጃ መውሰድ ሲጀምር ውጊያዎች መከሰታቸውን ቀጥለዋል (ለበለጠ መረጃ ኢፒኦ ከመጋቢት 23 እስከ ሚያዚያ 22, 2015 ወርሀዊ፡ የተቀረው የአገሪቱ ክፍል ሲረጋጋ በአማራ ክልል የተከሰተው አለመረጋጋት ይመልከቱ)። ይህ ሪፖርት በሚሸፍነው ጊዜ ውስጥ በኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት እና በፋኖ እና በአማራ ብሄር ታጣቂዎች መካከል ውጊያዎች በሰሜን ሸዋ ዞን በሸዋ ሮቢት፣ አንጾኪያ እና ደብረ ሲና እንዲሁም በኦሮሚያ ልዩ ዞን ማጀቴ ተመዝግበዋል (ከዚህ በታች ያለውን ካርታ ይመልከቱ)። በተጨማሪም የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት በሸዋ ሮቢት ከተማ እና ቆቦ ወረዳ የቤት ለቤት ፍተሻ አድርጓል።6 ከሚያዚያ 25 እስከ 26 በሰሜን ሸዋ ዞን በሸዋ ሮቢት እና በደብረ ሲና እንዲሁም በማዕከላዊ ጎንደር ዞን በጎንደር የመንግስትን እርምጃ በማውገዝ እና የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊትን እንቅስቃሴ ለመገደብ ተቃዋሚዎች መንገዶችን በድንጋይ ዘግተው ነበር።

በተጨማሪም በአማራ አመራሮች ላይ የሚፀመውን ግድያ በመቃወም በደቡብ ወሎ ዞን በደሴ፣ በኦሮሚያ ልዩ ዞን በከሚሴ ከተማ፣ በዋግ ኽምራ ዞን ሰቆጣ ሰላማዊ ተቃውሞ መደረጉ ተነግሯል። የደቡብ ወሎ ዞን አስተዳደር እንደገለጸው በዞኑ 21 ወረዳዎችና ከተሞች እንዲህ ዓይነት የተቃውሞ ሰልፎች ተካሂዷል።7
የአማራ ብልፅግና ፓርቲ ግንቦት 10 ቀን በክልሉ ወቅታዊ ሁኔታ እና የአማራ ህዝብ ጥያቄዎች ላይ ለመወያየት ያለመ ጉባኤ አካሂዷል። እንደ ክልሉ ፓርቲ ጽህፈት ቤት መሠረት 1,400 ከፍተኛ እና መካከለኛ አመራሮች በጉባኤው ላይ እንደሚገኙ ተገምቷል።8 በኮንፈረንሱ ማጠቃለያም በአማራ ክልል አንድነትን ለመፍጠር ኢኮኖሚያዊ፣ ፖለቲካዊ እና ማህበራዊ ጉዳዮችን ለመፍታት ተሳታፊዎቹ እቅድ አውጥተዋል። ኮንፈረንሱ በአማራ ክልል የሰሜን ግጭት ማብቃቱን ተከትሎ የሚካሄደውን መልሶ ግንባታ ለመደገፍ፣ ታጠቂ ኃይሎችን በሰላማዊ መንገድ ለማዋቀር፣ የአማራ ብሄር የሚያነሳቸውን እንደ ከድንበር ጋር እና ህገ-መንግስቱ ከማሻሻል ጋር የተያያዙ ጥያቄዎችን በሰላማዊ መንገድ በማንሳት ሁሉን አቀፍ ዴሞክራሲያዊ መንግስት ከሌሎች ኢትዮጵያውያን ጋር ለመመስረት በመስማማት ጨምሮ የአቋም መግለጫ በማውጣት ተጠናቋል።9
በጋምቤላ ክልል ከደቡብ ሱዳን የመጡ የሙርሌ ብሄረሰብ ታጣቂዎች ግንቦት 2 ቀን በአኝዋክ ዞን በጎግ ወረዳ የቀንድ ከብቶችን ለመዝረፍ ሲሞክሩ ከቀበሌ ታጣቂዎች ጋር ተዋግተዋል።
በትግራይ ክልል ግንቦት 6 ቀን በደቡብ ትግራይ ዞን አላማጣ ከተማ የራያ አላማጣ ነዋሪዎች ሰላማዊ ሰልፍ አደርገዋል። ተቃውሞ ሰልፉ የተካሄደው የኢትዮጵያ ብሄራዊ ምርጫ ቦርድ በሚቀጥለው አመት በክልሉ ስድስተኛውን ጠቅላላ ምርጫ ለማካሄድ ማቀዱን ይፋ ካደረገ በኋላ ነው ። ይህ ውሳኔ ራስን በራስ የማስተዳደር ጥያቄያቸውን ያላገናዘበ መሆኑን የገለጹት ሰልፈኞቹ ጥያቄያቸው ምላሽ ካላገኘ በምርጫው እንደማይሳተፉ አመላክተዋል። በሰሜን ኢትዮጵያ በተከሰተው ግጭት በክልሉ የተጎዱ የህዝብ መሠረተ ልማቶችን መልሶ ለመገንባት የሚያስፈልገውን በጀት መንግስት እንዲለቅም ጠይቀዋል።
በተጨማሪም የአለም ምግብ ፕሮግራም የምግብ ርዳታ “ያለአግባብ መበዝበዙ”10 ስላሳሰበው በክልሉ በሚያዚያ ወር እርዳታ መስጠት ቀንሷል። የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የሰብአዊ ጉዳዮች ማስተባበሪያ ፅህፈት ቤት (ዩኤንኦሲኤችኤ) በቅርቡ ያወጣው መረጃ እንደሚያመለክተው የእርዳታ ስርጭቱ “የምግብ ዕርዳታው በጣም የተቸገሩትን በብቃት ማዳረሱ ከተረጋገጠ በኋላ ይቀጥላል” ብሏል።11
በመጨረሻም በተለያዩ ክልሎች የሚገኙ የታጠቁ ኃይሎች በመንግስትን ጥሪ እና ከባህላዊ የሰላም አፈታት በኋላ ወደ ሰላማዊ ህይወት መመለሳቸውን ቀጥለዋል። በአማራ ክልል በአዊ ዞን ጃዊ ወረዳ የተካሄደውን ባህላዊ የሰላም ስምምነት ተከትሎ 118 የታጠቂ ቡድን አባላት ሚያዚያ 23 ቀን መሳሪያቸውን ከማስረከብ ይልቅ ጠመንጃቸውን ካስመዘገቡ በኋላ ወደ ሰላማዊ ህይወት ተመልሰዋል። ሚያዚያ 29 ቀን በምዕራብ ጎንደር ዞን ቋራ ወረዳ በአባይዳር፣ ባንባሆ እና ቀዝቀዝና ቀበሌዎች በዋናነት ይንቀሳቀሱ የነበሩ ከ80 በላይ የታጠቂ ቡድን አባላት ወደ ሰላማዊ ህይወት ለመመለስ ተስማምተዋል። በተመሳሳይ በቤንሻንጉል/ጉሙዝ ክልል 73 የጉሙዝ ታጣቂ ቡድን አባላት አለመግባባቶችን በድርድር ለመፍታት በመስማማት ተመልሰዋል።
Footnotes
- 2
አዲስ ማለዳ፣ ‘የኦሮሞ ነጻነት ሰራዊት” ቁልፍ በሆኑ የፖለቲከ ጉዳዮች ላይ መግባባት አልታቻለም አለ፣’ ሚያዚያ 25, 2015
- 3
አዲስ ማለዳ፣ ‘ኹለተኛው ምዕራፍ የኦነግ ሸኔ እና የመንግሥት ድርድር በቅርቡ እንደሚጀመር ተገለጸ፣’ ግንቦት 4, 2015
- 4
ኦኤልኤፍ-ኦኤልኤ፣ ‘የሰላም ንግግሮችን እና የገዢውን የቅርብ ጊዜ ጥቃቶች በተመለከተ (ኦኤልኤፍ-ኦኤልኤ ጋዜጣዊ መግለጫ)፣ ግንቦት 6, 2015
- 5
- 6
ቢቢሲ አማርኛ፣ ‘በአንዳንድ የአማራ ከተሞች እንቅስቃሴዎች መገታታቸውን እና የመከላከያ ሠራዊት መሰማራቱን ነዋሪዎች ተናገሩ፣’ ሚያዚያ 27, 2015
- 7
- 8
- 9
- 10
አሶስየትድ ፕሬስ፣ ‘የተባበሩት መንግስታት ድርጅት በስርቆት ምክንያት በኢትዮጵያ ለትግራይ የሚሰጠውን የምግብ እርዳታ አቆመ፣’ ሚያዚያ, 23, 2015
- 11