Skip to main content

ኢፒኦ ሳምንታዊ: ከሰኔ 10-16, 2015

ሰልፎች እና ግጭቶች በትግራይ እና ኦሮሚያ ክልሎች ተገልጠዋል።

29 June 2023

Also available in English

  • የፖለቲካ ግጭት ኩነቶች ብዛት - 1,105
  • በፖለቲካ ግጭቶች ምክንያት ሪፖርት የተደረጉ የሟቾች ቁጥር - 5,428
  • በሰላማዊ ሰዎች ላይ በተሰነዘሩ ጥቃቶች ምክንያት ሪፖርት የተደረጉ የሟቾች ቁጥር - 2,565
  • የፖለቲካ ግጭት ኩነቶች ብዛት - 21
  • በፖለቲካ ግጭቶች ምክንያት ሪፖርት የተደረጉ የሟቾች ቁጥር - 36
  • በሰላማዊ ሰዎች ላይ በተሰነዘሩ ጥቃቶች ምክንያት ሪፖርት የተደረጉ የሟቾች ቁጥር - 36

1

ኢትዮጵያን በተመለከተ በቁጥር የተደገፉ መረጃዎችን ከኢፒኦ የመረጃ መዝገብ እንዲሁም በዋናው የአክሌድ ኤክስፖርት መሳሪያ ውስጥ ማግኘት ይችላሉ።

በትግራይ ክልል የይገባኛል ጥታቄ በሚነሳባቸው አካባቢዎች የሚኖሩ የአማራ ተወላጆች የሚደረገው ሰልፍ ባለፈው ሳምንት የቀጠለ ሲሆን በኦሮሚያ ክልል ውጊያዎች እንዲሁም በሰላማዊ ሰዎች እና በመንግስት ባለስልጣናት ላይ ያነጣጠሩ ጥቃቶች ቀጥለዋል። በአማራ ክልልም በርካታ ሰልፎች ተካሄዱ ሲሆን ሰልፈኞች የተለያዩ ጥያቄዎችን አሰምተዋል።

ትግራይ ክልል የአማራ ተወላጆች በሰሜን ምዕራብ ትግራይ ዞን ዲማ እና ማይ ፀምሪ እንዲሁም በደቡብ ትግራይ ዞን አላማጣ ከተማ ሰልፎችን አደርገዋል (ከዚህ በታች ያለውን ካርታ ይመልከቱ )። መንግስት ለከተሞቻቸው የሚመድበውን በጀት ለትግራይ ክልል እንዳይለቅ እና ማንነትን መሰረት ያደረጉ የአስተዳደር ጥያቄዎቻቸውን እንዲፈታ ጠይቀዋል። በአሁኑ ወቅት ከተሞቻቸውን የሚያስተዳድረው የአማራ ክልል እንጂ የትግራይ ክልል አይደለም። ከአማራ ክልል ጋር የሚዋሰኑ የትግራይ ክልል አካባቢዎች የተለያዩ ብሔረሰቦች የሚኖሩበት ቢሆንም ከ1983 እስከ ጥቅምት 2013 ድረስ በትግራይ ክልል ስር በትግራይ ህዝብ ነፃነት ግንባር (ትህነግ/ህወሓት) ይተዳደሩ ነበረ።2 በዚያን ጊዜ በእነዚህ አካባቢዎች የሚኖሩ አማራዎች በአማራ ክልል ስር መተዳድር ፈልገው የነበረ ሲሆን ልክ ባለፈው ሳምንት እንደተመዘገቡት ሰልፎች ተመሳሳይ ሰልፎች ይካሄዱ ነበር። በሰሜን ኢትዮጵያ ግጭት ውቅት በሺዎች የሚቆጠሩ የትግራይ ተወላጆች በአማራ ታጣቂዎች በደረሰባቸው ጥቃት ከእነዚህ አካባቢዎች ተፈናቅለዋል። ባለፈው ሳምንት የዩናይትድ ስቴትስ ኤምባሲ ዲፕሎማቶች አላማጣን በመጎብኘታቸው የትግራይ ጊዜያዊ አስተዳደር ፕሬዝዳንትን ትችት የሰነዘሩ ሲሆን ጉብኝቱን “በትግራይ ክልል ላይ ህገ-ወጥ ወረራን እንደመደገፍ ነው” ሲሉ ተናግረዋል።3

ይህ በእንዲህ እንዳለ በሚያዚያ ወር የመንግስት እና የኦሮሞ ነጻነት ግንባር (ኦነግ)-ሸኔ ተወካዮች በታንዛኒያ እየተደረገ በነበረው የሰላም ኮንፈረንስ የተኩስ አቁም ሂደት ላይ ሳይስማሙ ከተመለሱበት በኃላ በኦሮሚያ ክልል የጀመረው ግጭት ቀጥሏል (የታንዛኒያውን የሰላም ንግግር ተከትሎ በኦሮሚያ ዳግም ስለተቀሰቀሰው ግጭት የበለጠ መረጃ ለማግኘት ኢፒኦ ከሚያዚያ 23 እስከ ግንቦት 23, 2015 ወርሀዊን ይመልከቱ )። ባለፈው ሳምንት በደቡብ ምዕራብ ሸዋ ዞን የሰደን ሶዶ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪን ኦነግ-ሸኔ እንደሆኑ የተጠረጠሩ ኃይሎች ለቀናት አግተው ለመልቀቅ ብር እንዲከፈላቸው ከጠየቁ በኃላ ዋና አስተዳዳሪውን ተኩሰው ገድለዋል። ሰኔ 10 ቀን ከኦነግ-ሸኔ ጋር ግንኙነት አላቸው የተባሉ ታጣቂዎች በሰሜን ሸዋ ዞን አሊ ዶሮ ቢያንስ 30 የከባድ መኪና ሹፌሮችን በማፈን የታፈኑትን ለመልቀቅ ብር ጠይቀዋል። ይህ ድርጊት በአማራ ክልል የተቃውሞ ስልፍ ቀስቅሷል። የኦነግ-ሸኔ ተወካዮች ግን በአፈናው ውስጥ እጃቸው እንዳሌሌበት በመጥቀስ አስተባብለዋል።4 በአማራ እና ኦሮሚያ ክልል አዋሳኝ በሚገኘው በሰሜን ሸዋ ዞን የከባድ መኪና አሽከርካሪዎች ላይ አፈና እና ጥቃት አልፎ አልፎ የሚከሰት ሲሆን ባለፈው አንድ አመት በርካታ አሽከርካሪዎች በአካባቢው ተገድለዋል።

በተጨማሪም በኦሮሚያ ክልል የመንግስት ኃይሎች የኦነግ-ሸኔ ደጋፊዎች ናቸው ያሏቸውን በጥይት ተኩሰው ገድለዋል። በገንጂ ጎሮ ሆሬ ቀበሌ የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት ኦነግ-ሸኔን ይደግፋሉ በሚል ክስ አራት የአንድ ቤተሰብ አባላት የሆኑ ሰላማዊ ሰዎችን ተኩሶ ገድሏል። በሌላ በኩል በምዕራብ ጉጂ ዞን መልካ ሶዳ ወረዳ በዳዋ ከተማ የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት ኃይሎች ሁለት ወጣቶችን ተኩሰው ገድለዋል።5 እነዚው ወጣቶች ኦነግ-ሸኔን በመደገፍ ተጠርጥረው ከአንድ ቀን በፊት ታስረው ነበር።

ባለፉት ሁለት ሳምንታት በኦሮሚያ ክልል ሰሜን ምዕራብ ክፍል በኦነግ-ሸኔ እና በአካባቢው የአማራ ታጣቂዎች መካከል ውጊያ እንዲሁም በሰላማዊ ሰዎች ላይ ያነጣጠረ ጥቃት የተከሰተ ሲሆን ግጭቶች በምስራቅ ወለጋ ዞን ኪረሙ እና በሆሮ ጉዱሩ ወለጋ ዞን አሙሩ ውስጥ ተከስተዋል። ከህዳር 2015 በኃላ በኦሮሙያ ሰሜናዊ ምዕራብ አካባቢ የፖለቲካ ግጭት ጨምሯል (በኦሮሚያ እየጨመረ ስላለው ግጭት እና እየተፋፋ ያለበትን ስፍራዎች ላይ የበለጠ መረጃ ለማግኘት ኢፒኦ ከሕዳር 22 እስከ ታህሳስ 22, 2015 ወርሃዊ እና ኢፒኦ ከጥቅምት 22 እስከ ሕዳር 21, 2015 ወርሃዊ ይመልከቱ )።

በመጨረሻም በአማራ ክልል አርሶ አደሮች ሰኔ 12 ቀን በምዕራብ ጎጃም ዞን በባህር ዳር ከተማ በክልሉ አስተዳደርና ግብርና ቢሮ ፊት ለፊት የተቃውሞ ሰልፍ አድርገዋል። ሰልፈኞቹ የአካባቢው ባለስልጣናት የማዳበሪያ ፍላጎቶችን እንዲፈቱ የጠየቁ ሲሆን መንግስት ማዳበሪያውን ወደ ግል ነጋዴዎች እያስተላለፈ ነው ሲሉ ከሰዋል።6 በተመሳሳይ ቀን በምስራቅ ጎጃም ዞን በአማኑኤል ከተማም ሌላ ተቃውሞ ተካሂዷል። የከባድ መኪና አሽከርካሪዎች በኦሮሚያ ክልል አሊ ዶሮ ታፍነው ከተወሰዱ በኋላ መንግስት ሰላማዊ ሰዎችን የመጠበቅ ኃላፊነቱን እንዲወጣ ሰልፈኞቹ ጠይቀዋል። የአማራ ክልል ፖሊስ ተቃዋሚዎችን ለመበተን ጥይት በመተኮሱ የአንድ ሰው ህይወት ማለፉን እና አራት ሰዎችን ማቁሰሉ ተነግሯል። ከጥቂት ቀናት በኋላ ሰኔ 15 ቀን በደቡብ ወሎ ዞን በደላንታ ወረዳ ሰልፈኞች እንድ ቀን ቀደም ብሎ በኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት ወታደር የተፈፀመውን የህፃን ልጅ መደፈር በማውገዝ የመንግስት ኃይሎች ከተማዋን ለቀው እንዲወጡ ጠይቀዋል። ሰልፉ ከመደረጉ አንድ ቀን ቀደም ብሎም በተመሳሳይ ከተማ በኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት ኃይሎች እና በፋኖ ታጣቂዎች መካክል ውጊያ መደረጉ ተዘግቦ ነበር።

Country
Ethiopia
Region
Africa
Share on

Related content