Skip to main content

ኢፒኦ ሳምንታዊ: ከጥር 27–የካቲት 3, 2015

Summary of events in Ethiopia from Tir 27, 2014 – Yekatit 3, 2015, including political conflicts and social unrest.

15 February 2023

Also available in English

በቁጥር: ኢትዮጵያ, ከጥር 27, 2014 – የካቲት 3, 2015

  • የፖለቲካ ግጭት ኩነቶች ብዛት: 1,241
  • በፖለቲካ ግጭቶች ምክንያት ሪፖርት የተደረጉ የሟቾች ቁጥር: 6,613
  • በሰላማዊ ሰዎች ላይ በተሰነዘሩ ጥቃቶች ምክንያት ሪፖርት የተደረጉ የሟቾች ቁጥር: 2,638

በቁጥር: ኢትዮጵያ, ከጥር 27–የካቲት 3, 20151

  • የፖለቲካ ግጭት ኩነቶች ብዛት: 12
  • በፖለቲካ ግጭቶች ምክንያት ሪፖርት የተደረጉ የሟቾች ቁጥር: 28
  • በሰላማዊ ሰዎች ላይ በተሰነዘሩ ጥቃቶች ምክንያት ሪፖርት የተደረጉ የሟቾች ቁጥር: 14

ኢትዮጵያን በተመለከተ በቁጥር የተደገፉ መረጃዎችን ከኢፒኦ የመረጃ መዝገብ እንዲሁም በዋናው የአክሌድ ኤክስፖርት መሳሪያ ውስጥ ማግኘት ይችላሉ።

የሁኔታዎች አጭር መግለጫ

የኢትዮጵያ ፖለቲካ ምህዳር ባለፈው ሳምንት በኦርቶዶክስ ቤተ-ክርስቲያን ውስጥ ባለው መከፋፈል ጋር በተገናኘ ግጭት የተከበበ የነበረ ሲሆን አብዛኛው ግጭት በኦሮሚያ ክልል ተከስቷል። በአማራ ክልል መጠነኛ ውጊያ መከሰቱ የተገለጸ ሲሆን የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት በትግራይ የሚገኙ ሁለት ዞኖችን በሰላማዊ መንገድ ለትግራይ ህዝብ ነፃነት ግንባር (ትህነግ/ህወሓት) አስረክቧል።

በኦሮሚያ ክልል ምዕራብ አርሲ ዞን በሻሸመኔ ከተማ በቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን ‘በሕገወጥ መንገድ’ ተሾሙ የተባሉት ጳጳሳት መምጣትን በመቃወም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን (ኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ) ተከታዮች በጥር 27, 2015 የቤተክርስቲያኑን ደወል በመደወል ምዕምናን ቤተክርስቲያንን እንዲጠብቁ ጥሪ በማደረጓ ምዕምናን ወጥተው ‘በሕገወጥ መንገድ’ ተሾሙ የተባሉት ጳጳሳትን ተቃውመዋል። የኦሮሚያ ክልል ልዩ ኃይል በኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ ህገ-ወጥ ነው የሚባለው የአዲሱ የኦሮሚያ ሲኖዶስ ደጋፊዎች ጋር በመሆን ኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ ደጋፊ ምዕምናን ወደ ቤተክርስቲያኑ እንዳይገቡ የቤተክርስቲያኑን በር በመዝጋት ህዝቡን ለመበተን ተኩስ ከፍተዋል። የኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ ደጋፊ ምዕምናን የፖሊስ ኃይሎችን እና ደጋፊዎቻቸውን እየገፉ በዱላ እየመቱ የቤተክርስቲያኑ ቅጥር በማፍረስ ወደ ግቢ ገብተዋል። የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን እንደገለፀው ቢያንስ ስምንት ሰዎች ተገድለዋል።2 የኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ 13 ሰዎች ሞተዋል ብሏል። በጥቃቱ የተጎዱ ከ40 ያላነሱ ሰዎች ወደ ሀዋሳ ሆስፒታል እንደተወሰዱ ተነግሯል።3

በተመሳሳይ የኦሮሚያ ክልል ልዩ ኃይል፣ የክልሉ ፖሊስ እና የአካባቢ ታጣቂዎች ሰላማዊ ሰዎችን በመደብደብ እና በኦሮሚያ ክልል በተለያዩ ቦታዎች የሚገኙ የኦርቶዶክስ አብያተ ክርስቲያናት ባለስልጣናትን በማስገደድ አብያተ ክርስቲያናት ለአዲሱ የኦሮሚያ ሲኖዶስ ባለስልጣናት እንዲረከቡ አድርገዋል ተብሏል (ከዚህ በታች ያለውን ካርታ ይመልከቱ)። ጥር 29 ቀን በምዕራብ ጉጂ ዞን ቡሌ ሆራ ከተማ እና በኦሮሚያ በምስራቅ ሸዋ ዞን አዳማ ከተማ የኦሮሚያ ልዩ ኃይል እና የኦሮሚያ ክልል ፖሊስ አባላት የኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን ሲኖዶስ ያቀረበውን ጥሪ ተከትሎ ጥቁር ልብስ ለብሰው የነበሩ የኦርቶዶክስ ተዋህዶ ምዕመናንን ደብድበዋል። ወደ ደብረ ገነት ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያንም በኃይል ገብተው ቤተክርስቲያኗን ለኦሮሚያ ሲኖዶስ ተሿሚዎች አስረክበዋል። የካቲት 2 ቀን በኦሮሚያ በሸገር ከተማ በወለቴ ዮሃንስ ቤተክርስቲያን ቤተክርስቲያኒቷ በኦሮሚያ ሲኖዶስ አንዳትወሰድ ለመጠበቅ በተሰበሰቡ የኦርቶዶክስ ተዋህዶ ተከታዮች ላይ የኦሮሚያ ክልል ልዩ ኃይል ተኩስ ከፍቷል።

የኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ ባለስልጣናት ከጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ ጋር ያደረጉትን ውይይት ተከትሎ ሊካሄድ የታቀደውን ህዝባዊ ተቃውሞ ለሌላ ጊዜ ማስተላለፍ ቢቻልም በሀገሪቱ ውጥረቱ ቀጥሏል።4 ለጊዜው የኢትዮጵያ ፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት የኦሮሚያ ሲኖዶስ አባላት ወደ የትኛውም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ደብር ወይም ቤተ ክርስቲያን እንዳይገቡ የሚከለክል የእግድ ትእዛዝ የኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ ደግፎ ሰጥቷል። በተጨማሪም ፍርድ ቤቱ ውሳኔውን እንዲያስፈፅሙ ለሰላም ሚኒስቴር፣ ለፌዴራል ፖሊስ፣ ለኦሮሚያ ክልል እና ለኦሮሚያ ፖሊስ ኮሚሽን ትዕዛዝ ሰጥቷል።5 የካቲት 1 ቀን የኦሮሚያ፣ የሀረሪ እና የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልሎች ያልተፈቀደ ሰልፍ የሚከለክል መግለጫ አውጥተዋል።6

በሳምንቱ ውስጥ አዲስ የተቋቋመውን የኦሮሚያ ሲኖዶስ የሚደግፍ ሰልፎች በጅማ ከተማ የተካሄዱ ሲሆን በሌላ በኩል የኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክን በመደገፍና የኦሮሚያ ሲኖዶስን በመቃወም በኦሮሚያ ክልል በአርሲ ዞን አሰላ እና በአማራ ክልል ሰሜን ጎንደር ዞን ደባርቅ ተካሂደዋል።

በአማራ ክልል ጥር 28 ቀን በቀበሌ ታጣቂዎች እና በትህነግ/ህወሓት ኃይሎች መካከል ጦርነት መካሄዱ ተዘግቧል። በዋግ ኽምራ ዞን ፅጊብጂ ወረዳ በጥራሪ ወንዝ እና በወዲ ገብሩ አካባቢ በነበረው ውጊያ ቢያንስ ሁለት ሰዎች መሞታቸው ተዘግቧል። አሁንም በትህነግ/ህወሓት ሃይሎች ቁጥጥር ስር በሚገኙትን እነዚህን አካባቢዎች መልሶ ለመቆጣጠር በማሰብ የአካባቢው ታጣቂዎች ወደ አካባቢው ከገቡ በኋላ ጦርነቱ ተቀስቅሷል። የዋግ ኽምራ ዞን በግጭቱ ከፍተኛ ጉዳት ከደረሰባቸው አካባቢዎች አንዱ ሲሆን እ.አ.አ እስከ ጁላይ 2022 ድረስ ከአንድ አመት በላይ ከሰብአዊ እርዳታ ተቋርጦ ነበር።7 በዋግ ኽምራ ዞን አበርገሌ እና ፀጊብጂ ወረዳዎች ከ67,000 በላይ ነዋሪዎች አፋጣኝ ሰብዓዊ እርዳታ እንደሚያስፈልጋቸው አንድ ሪፖርት ያመላክታል።8 በሌላ የክልሉ ስፍራ፣ በምስራቅ ጎጃም ዞን መቸከል ወረዳ ጥር 27 ቀን ማንነታቸው ያልታወቁ ታጣቂዎች ከወረዳው ሰላምና ፀጥታ ጽ/ቤት ኃላፊ እና ከወረዳ ሚሊሻ ጽ/ቤት ኃላፊ ጋር ከተዋጉ በኃላ ሁለቱ ኃላፊዎችን ተገድለዋል። እስከ አሁን ለዚህ ክስተት ኃላፊነቱን የወሰደ አካል የለም።

በጋምቤላ ክልል የካቲት 1 ቀን ከደቡብ ሱዳን የመጡ የሙርሌ ብሄረሰብ ታጣቂዎች ድንበር ጥሰው በአኝዋክ ዞን በጎግ  ወረዳ አተቲ ቀበሌ በሚገኘው ኡቱዩ መንደር በሰላማዊ ሰዎች ላይ ጥቃት ሰንዝረዋል። እነዚህ ታጣቂዎች ሁለት ሰላማዊ ሰዎችን ገድለው አንድ ሰው አቁስለዋል ተብሏል። በማግስቱ 50 የሚሆኑ የሙርሌ ብሄረሰብ ታጣቂዎች በአቦቦ ወረዳ አቦቦ ከተማ አቅራቢያ በሚገኝ ባለ ባለሃብት እርሻ በመግባት ፍየሎችን ጨምሮ ንብረት ከዘረፉ በኋላ ከክልሉ የጸጥታ ኃይሎች ጋር ተዋግተዋል።9 በሰላማዊ  ሰዎች ላይ ድንበር ዘለል ጥቃት በአኝዋክ ዞን አልፎ አልፎ የሚከሰት ሲሆን በጥቅምትና ህዳር 2015 ሁለት ገዳይ የሆኑ ክስተቶች ሪፖርት ተደርገዋል።

በትግራይ ክልል ጠቅላይ ሚንስትር አብይ ከትህነግ/ህወሓት ተደራዳሪዎች ጋር ከተገናኙ በኋላ የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት የማዕከላዊ እና ሰሜን ምዕራብ ትግራይ ዞኖችን ለትህነግ/ህወሓት ባለስልጣናት አሳልፎ ሰጥቷል።10 ባለፈው ሳምንት በትግራይ የባንክ አገልግሎትም ወደ ነበረበት የተመለሰ ሲሆን በ2013 የፌዴራል መንግስት ኃይሎች ከክልሉ ከወጡ በኋላ የባንክ አገልግሎት ላላገኙት ዜጎች እፎይታን ፈጥሯል።11

በደቡብ ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ክልል በጋሞ፣ ወላይታ፣ ጎፋ፣ ጌዲኦ፣ ኮንሶ እና ደቡብ ኦሞ ዞኖች እንዲሁም በአምስት ልዩ ወረዳዎች – ቡርጂ፣ አማሮ፣ ደራሼ፣ ባስኬቶ እና አሌ – ውስጥ እነዚህን ዞኖች እና ልዩ ወረዳዎችን ያቀፈ አዲስ ክልላዊ መንግስት ለመመስረት የሚያስችል ህዝበ ውሳኔ ተካሂዷል። በአብዛኛዎቹ አካባቢዎች ምርጫው ያለምንም ችግር ተጠናቋል። በወላይታ ዞን ሶርቶ ቀበሌ የቀበሌው አስተዳደር ባለስልጣናት 105 መታወቂያዎችን ለመራጮች ሲያከፋፍሉ በመታየቱ በኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የድምጽ አሰጣጥ ሂደቱ ለተወሰኑ ሰዓታት እንዲቆም ተደርጓል።12 ፖሊስ ከዚህ ክስተት ጋር በተያያዘ ሁለት ግለሰቦችን ካሰረ በኋላ ድምጽ መስጠት ሂደቱ እንዲቀጥል ተደርጓል።13 ህዝበ ውሳኔው12ኛውን ክልል የመመስረት እድሉ ከፍተኛ ነው።

Footnotes

  1. 1

    በዚህ የጊዜ ገደብ ውስጥ የተከሰቱ አንድ አንድ ኩነቶች በዘገባ መዘግየት ምክንያት በቀጣይ ሳምንታት ውስጥ በመረጃ ቋታችን ውስጥ ሊካተቱ ይችላሉ።

  2. 2

    የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን፣ ‘የሰብአዊ መብቶች ጥሰቶች ሳይባባሱ አፋጣኝ መፍትሔ የማፈላለጉ ሥራ ሊጠናከር ይገባል፣’ የካቲት 3, 2015

  3. 3

    ኢኤምኤስ፣ ‘ኢኤምኤስ መረጃ እሮብ የካቲት 1, 2015፣’ የካቲት 1, 2015

  4. 4

    ፊሊፕ ኤ ቸርም፣ ‘የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ መሪዎች በከፍተኛ ደረጃ የተጠራውን ተቃውሞ ለሌላ ጊዜ አስተላልፈዋል፣’ አፍሪካ ኒውስ፣ የካቲት 5, 2015

  5. 5

    የኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ ብሮድካስቲንግ አገልግሎት ኤጀንሲ፣ የካቲት 3, 2015

  6. 6

    አዲስ ስታንዳርድ፣ ‘ዜና፡ የኦሮሚያ፣ የሀረሪ እና የደቡብ ምዕራብ ክልሎች የጋራ ግብረ ሃይል ሰልፎችን ለመከልከል የወሰነውን ውሳኔ እንደሚደግፉ ገለጹ፣ ኦሮሚያ “ትዕግስት አልቋል” አለ’ የካቲት 3, 2015

  7. 7

    አዲስ ስታንዳርድ፣ ‘ዜና፡ በዋግ ኽምራ ዞን ከአንድ አመት በኃላ የመጀመሪያ እርዳታ ኮንቮይ ተቀበለ፣’ ሐምሌ 20, 2014

  8. 8

    አበበ ፍቅር፣ ‘በአማራ ክልል በዋግ ሕምራ ብሔረሰብ ልዩ ዞን ከ67 ሺሕ በላይ ዜጎች ለከፋ ረሃብ መጋለጣቸው ተሰማ፣’ ሪፖርተር፣ ታህሳስ 26, 2015

  9. 9

    የጋምቤላ ክልል መንግስት ፕሬስ ሴክሬታሪያት ጽ/ቤት፣ ‘ከደቡብ ሱዳን ተነስተው በጋምቤላ ክልል ጎግ ወረዳ አተቲ ቀበሌ ጉዳት ያደረሱ የሙርሌ ጎሳ ታጣቂዎች ላይ ክትትል እየተደረገ እንደሚገኝ የክልሉ ሰላምና ፀጥታ ቢሮ አስታወቀ፣’ የካቲት 2, 2015

  10. 10

    ሮይተርስ፣ ‘የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር ከሰላም ስምምነት በኋላ ለመጀመሪያ ጊዜ ከትግራይ ክልል መሪዎች ጋር ተገናኙ።’ የካቲት 26, 2015

  11. 11

    ዲደብሊው አማርኛ፣ ‘ባንኮች በትግራይ የተሟላ አገልግሎት መስጠት ጀመሩ፣’ የካቲት 1,፣ 2015

  12. 12

    የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ፣ ጥር 29, 2015

  13. 13

    የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ፣ ጥር 29, 2015

Country
Ethiopia
Region
Africa
Share on

Related content