Skip to main content

ኢፒኦ ሳምንታዊ: ከጥር 6-12, 2015

Overview of political conflicts and incidents in Ethiopia during January 6-12, 2015.

25 January 2023

Also available in English

በቁጥር: ኢትዮጵያ, ከጥር 6, 2014 –ጥር 12, 2015

  • የፖለቲካ ግጭት ኩነቶች ብዛት: 1,264
  • በፖለቲካ ግጭቶች ምክንያት ሪፖርት የተደረጉ የሟቾች ቁጥር: 6,515
  • በሰላማዊ ሰዎች ላይ በተሰነዘሩ ጥቃቶች ምክንያት ሪፖርት የተደረጉ የሟቾች ቁጥር: 2,702

በቁጥር: ኢትዮጵያ, ከጥር 6-12, 20151

  • የፖለቲካ ግጭት ኩነቶች ብዛት: 13
  • በፖለቲካ ግጭቶች ምክንያት ሪፖርት የተደረጉ የሟቾች ቁጥር: 17
  • በሰላማዊ ሰዎች ላይ በተሰነዘሩ ጥቃቶች ምክንያት ሪፖርት የተደረጉ የሟቾች ቁጥር: 9

ኢትዮጵያን በተመለከተ በቁጥር የተደገፉ መረጃዎችን በኢፒኦ የዳታ ፋይል እንዲሁም በዋናው የአክሌድ ኤክስፖርት መሳሪያ ውስጥ ማግኘት ይችላሉ።

የሁኔታዎች አጭር መግለጫ

ባለፈው ሳምንት በኦሮሚያ ክልል በመንግስት ኃይሎች – በኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት እና በኦሮሚያ ክልል ልዩ ኃይል – እና በኦሮሞ ነጻነት ግንባር (ኦነግ)-ሸኔ መካከል የሚደረጉ ውጊያዎች የቀጠሉ ሲሆን የኤርትራ ወታደሮች ከትግራይ ክልል ቁልፍ ከተሞች ለቀው ወጥተዋል። በኦሮሚያ ክልል በምዕራብ ሸዋ ዞን በሊበን ጃዊ ወረዳ በጋሞ ወሊሶ እና ባዳ ጎራ ቀበሌዎች እና በዳኖ ወረዳ ስዮ አካባቢ በመንግስት ታጣቂዎች እና በኦነግ-ሸኔ መካከል ውጊያዎች ተመዝግቧል (ከዚህ በታች ያለውን ካርታ ይመልከቱ)። በእነዚህ አካባቢዎች ሁለቱ ወገኖች ከጥር 3 እስከ 7 ድረስ ለአምስት ቀናት ተዋግተዋል።

ጥር 11 ቀን የኦነግ-ሸኔ አባላት በሰሜን ሸዋ ዞን ሙኬ ጡሪ ከተማ በመግባት ሁለት ፖሊሶችን ገድለዋል። እነዚህ ፖሊሶች የተገደሉት በኦነግ-ሸኔ አባላት እየተፈፀመ የነበረውን የአካባቢው ነዋሪዎች ንብረት ዘረፋን ለማስቆም ሲሞክሩ ነበር። ከጥር 5 እስከ 8 ባለው ጊዜ ውስጥ በኦሮሚያ ክልል በምስራቅ ሐረርጌ ዞን ጭናቅሰን ወረዳ በቱሉ ጉሌድ፣ በፈፌም፣ በጨፌ ባዱ፣ በመራር እና በሆሳሌ ቀበሌዎች የሶማሌ ብሔር ታጣቂዎች ከኦሮሞ ብሔር ታጣቂዎች ጋር ተዋግተዋል። በእነዚህ ውጊያዎች ሶስት ታጣቂዎች ሲገደሉ ሌሎች ስምንት ቆስለዋል።

የኢትዮጵያ መንግስት ኮሙዩኒኬሽን ሚኒስትር ባለፈው ሳምንት እንዳስታወቁት በኦሮሚያ ክልል እና በአጎራባች ክልሎች የበለጠ መረጋጋትን ለማምጣት መንግስት በኦነግ-ሸኔ ላይ ፖለቲካዊ እና ወታደራዊ እርምጃዎችን ያካተቱ “ሁሉን አቀፍ እርምጃ” እየወሰደ ነው።2 እንደ ሚኒስትሩ ገለጻ መንግስት በሰላማዊ መንገድ እጃቸውን የሰጡ የቡድኑን አባላት የተሃድሶ ስልጠና ስጥቶ ወደ ህብረተሰቡ ለመመለስ ዝግጁ መሆኑን እና የመንግስትን ጥሪ ለመቀበል ፈቃደኛ ባልሆኑ ላይ ደግሞ ወታደራዊ እርምጃ ይወስዳል። ሚኒስትሩ ቀደም ሲል ላልተሳኩ ግጭቱን በሰላማዊ መንገድ ለመፍታት የተደረጉ ሙከራዎች ኦነግ-ሸኔን ተጠያቂ አድርገዋል። በህዳር ወር የኦሮሚያ ክልል ባለስልጣናት ኦነግ-ሸኔ “አንድ ወጥ የእዝ ሰንሰለት” ስለሌለው እና “ቦታን ተከትሎ በቡድኑ ውስጥ ባለው ክፍፍል” እንዲሆም ቡድኑ “አላማና አመራር አደረጃጀት የጎደለው እና ያልተደራጀ በመሆኑ” ከኦነግ-ሸኔ ጋር እንደማይደራደሩ ጠቁመው ነበር።3 ኦነግ-ሸኔ በሰጠው ምላሽ ከፌዴራል መንግስት ጋር በገለልተኛ እና በሶስተኛ ውገን በኩል ብቻ እንደሚደራደር እና “በገዥው ካድሬዎች – ማንኛውም የሽምግልና ማዕረግ ይዘው ቢመጡ – ምንም አይነት ድርድር እንደማይሰራ” አስታውቋል።4

ባለፈው ሳምንት በኦሮሚያ በሰላማዊ ሰዎች ላይ የሚደርሰው ጥቃት የቀጠለ ሲሆን በክልሉ ሶስት እንደዚህ ያሉ የጥቃት ኩነቶች ተመዝግበዋል። እነዚህ ጥቃቶች የተፈፀሙት በኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት፣ በኦሮሚያ ክልል ልዩ ኃይል፣ በቀበሌ ታጣቂዎች እና በፋኖ ታጣቂዎች ነው። ጥር 6 ቀን በምዕራብ ሸዋ ዞን ኢፋታ (ኢልፈታ) ወረዳ በሶምቦ ቺቱ እና በሂዳቡ ሲንዲ ቀበሌዎች በሰላማዊ ሰዎች መኖሪያ ቤቶች ላይ የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት እና የኦሮሚያ ልዩ ኃይል አባላት ናቸው ተብሎ የተገመቱ የመንግስት ታጣቂዎች ተኩስ ከፍተው የርካታ የሰላማዊ ሰዎች ቤቶችን አቃጥሏል። ከጥቂት ቀናት በኋላ ጥር 10 ቀን በምስራቅ ሸዋ ዞን ቦሰት ወረዳ ቦፋ (ዋርጂ) ከተማ የቀበሌ ታጣቂዎች እንደሆኑ የሚገመቱ ታጣቂዎች አምስት እስረኞችን ከእስር ቤት ካወጡ በኋላ ተኩሰው ገድለዋል። ከእነዚህ ጥቃቶች በስተጀርባ ያለው ምክንያት አልታወቅም። ጥር 6 አካባቢም የፋኖ ታጣቂዎች በሰሜን ሸዋ ዞን ደራ ወረዳ ሰራር ኩላ (ሰለልኩላ) ቀበሌ ከኦነግ-ሽኔ ጋር ተባብረዋል በሚል ቁጥራቸው በውል ያልታወቀ ሰላማዊ ሰዎችን በጥይት ተኩሰው መግደላቸውም ተዘግቧል።

ትግራይ ክልል ጥር 9 ቀን የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዎት በምስራቅ ትግራይ ዞን አዲግራት ከተማ በሰላም በመግባት የከተማው የሚገኘውን ወታደራዊ ካምፕ ተቆጣጥሯል። የትግራይ ህዝብ ነፃነት ግንባር (ትህነግ/ህወሓት) ኃይሎች በጥር 5 ቀን ከከተማው ለቀው መውጣታቸው ተነግሯል። በተጨማሪም ከጥር 10 ጀምሮ የኤርትራ መከላከያ ሠራዊት ከትግራይ ክልል ከአድዋ፣ አክሱምና ሽሬ ከተሞች እንዲሁም ፈላፊል እና እንደባገሪማ አካባቢዎች መውጣት መጀመሩን በርካታ ዘገባዎች ያመላክታሉ።5 የአፍሪካ ህብረት አደራዳሪ ቡድን መሪ የቀድሞ የናይጄሪያ ፕሬዝዳንት ኦሉሴጎን ኦባሳንጆ የኤርትራ መከላከያ ሠራዊት ከትግራይ ክልል መውጣት መጀመሩን እና አሁን “ሁሉም ኤርትራዊያን በድንበር ላይ ናቸው” በማለት የተናገሩ ሲሆን “ሁሉም ወደ ሀገራቸው እንዳልተመለሱ” ግን አምነዋል።6 የትህነግ/ህወሓት ቃል አቀባይ አቶ ጌታቸው ረዳ ግን ይህንን መግለጫ ውድቅ በማድረግ የአፍሪካ ህብረት ክትትል፣ ማረጋገጫ እና ተገዢ ተልዕኮ “እንዲህ አይነት አስተያየት ከመስጠታቸው በፊት ስራቸውን እንዲሰሩ” ጠይቀዋል።7 ይህ በእንዲህ እንዳለ የኢትዮጵያ መንግስት ኮሙዩኒኬሽን ሚኒስተር አንዳንድ የትህነግ/ህወሓት ከፍተኛ አመራሮች “የመንግስት ኃይሎችን የሚያወግዙ እና የጎረቤት ክልል ኃይሎችን አጥፊ እና የትህነግ/ህወሓት ኃይሎች ንፁሀን” የሚያደርጉ አሉታዊ መግለጫዎችን ከመስጠት እንዲቆጠቡ ጠይቋል።8 እሳቸው እንደሚሉት እንዲህ ያሉት መግለጫዎች በጥቅምት ወር መጨረሻ የተፈረመውን የሰላም ስምምነት መንፈስ ይቃረናሉ።

በመጨረሻም በቤንሻንጉል / ጉሙዝ ክልል አሶሳ ዞን በአብራሞ ወረዳ በየምባ ሲዚም ቀበሌ የቤንሻንጉል ህዝቦች ነፃነት ንቅናቄ ንዑስ ቅርንጫፍ ጽ/ቤት የመክፈቻ ስነ ስርዓት ላይ በአብራሞ ወረዳ ስር የሚገኙ የቀበሌ ታጣቂዎች የቤኒሻንጉል ህዝቦች ነፃነት ንቅናቄ አባልን ተኩሰው ገድለዋል። በጥቃቱ ሌሎች ሰባት ሰዎች ቆስለዋል።

Footnotes

  1. 1

    በዚህ የጊዜ ገደብ ውስጥ የተከሰቱ አንድ አንድ ኩነቶች በዘገባ መዘግየት ምክንያት በቀጣይ ሳምንታት ውስጥ በመረጃ ቋታችን ውስጥ ሊካተቱ ይችላሉ።

  2. 2

    ኢቢሲ፣ ጥር 10, 2015

  3. 3

    አዲስ ስታንዳርድ፣ ሕዳር 20, 2015

  4. 4

    ቲዊተር @ኦዳታርቢደብሊውቢኦ፣ ሕዳር 20, 2015

  5. 5

    ቢቢሲ አማርኛ፣ ጥር 12, 2015

  6. 6

    ፋይናሻል ታይምስ፣ ጥር 7, 2015

  7. 7

    ቲዊተር @ረዳ_ጌታቸው፣ ጥር 9, 2015

  8. 8

    ኢቢሲ፣ ጥር 10, 2015

Country
Ethiopia
Region
Africa
Share on

Related content