- የፖለቲካ ግጭት ኩነቶች ብዛት: 1,216
- በፖለቲካ ግጭቶች ምክንያት ሪፖርት የተደረጉ የሟቾች ቁጥር: 6,470
- በሰላማዊ ሰዎች ላይ በተሰነዘሩ ጥቃቶች ምክንያት ሪፖርት የተደረጉ የሟቾች ቁጥር: 2,590
- የፖለቲካ ግጭት ኩነቶች ብዛት: 3
- በፖለቲካ ግጭቶች ምክንያት ሪፖርት የተደረጉ የሟቾች ቁጥር: 37
- በሰላማዊ ሰዎች ላይ በተሰነዘሩ ጥቃቶች ምክንያት ሪፖርት የተደረጉ የሟቾች ቁጥር: 2
ኢትዮጵያን በተመለከተ በቁጥር የተደገፉ መረጃዎችን ከኢፒኦ የመረጃ መዝገብ እንዲሁም በዋናው የአክሌድ ኤክስፖርት መሳሪያ ውስጥ ማግኘት ይችላሉ።

የሁኔታዎች አጭር መግለጫ
ባለፈው ሳምንት የኢትዮጵያ የፖለቲካ ሁኔታ በአንጻራዊ የተረጋጋ ነበር። አክሌድ ባለፈው ሳምንት ከኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት (መጅሊስ) ጋር በተያያዘ ሁለት ኩነቶችን – በኦሮሚያ ክልል የተከሰተ ረብሻን እና በአማራ ክልል የተካሄደ ተቃውሞን – ጨምሮ በሀገሪቱ አራት ያለመረጋጋት ኩነቶችን ብቻ መዝግቧል። የተቀሩት ሁለቱ ኩነቶች በኦሮሚያ ክልል በሰላማዊ ሰዎች ላይ የተፈፀመ ጥቃት ኩነትን እና በሶማሌ ክልል የተከሰተ የውጊያ ኩነትን ያካትታሉ (ከዚህ በታች ያለውን ካርታ ይመልከቱ)።

በኦሮሚያ ክልል በምስራቅ ወለጋ ዞን በነቀምት ከተማ የካቲት 12 ቀን ሙስሊም ሰልፈኞች ፍትህ መስጊድ በመግባት አዲስ የተሾሙ የመጅሊስ አባላት የሶላት ንግግር እንዳያደርጉ ከልክለዋል። በመቀጠልም ቡድኑ በመስጊዱ የተገኙትን በመደብደብ እና መስኮቶችን በመስበር ጉዳት አድርሷል። በከተማው የሰፈረው የኮማንድ ፖስት ኃይሎች ጣልቃ በመግባት ሁኔታውን ማረጋጋት ችለዋል። ከሳምንት በፊት የካቲት 3 ቀን በከተማዋ የሚገኘውን ትልቁን መስጊድ ለአዲሱ መጅሊስ ለማስረከብ ፈቃደኛ ባለመሆናቸው ሰባት ሙስሊም የሀገር ሽማግሌዎችና የኃይማኖት ሙሁራን ታስረው ነበር።2
በነቀምት የሚኖሩ የሱፊ ሙስሊሞች አዲሱን መጅሊስ ብጥብጥ በመቀስቀስ የወነጀሉ ሲሆን መጅሊሱ “በወሃቢ ቡድን የበላይነት የተያዘ ነው” ሲሉም ወቅሰዋል።3 በአዲስ አበባ፣ በሐረር፣ በኢሉ አባ ቦራ፣ በጅማ እና በአዳማ ተመሳሳይ አለመግባባቶች በሙስሊሙ ማህበረሰብ ውስጥ እንደሚገኝ ተዘግቧል።4 በአማራ ክልል በደቡብ ወሎ ዞን በኮምቦልቻ ከተማ የካቲት 12 ቀን የኮምቦልቻ ከተማ ሙስሊም ነዋሪዎች “መጅሊሱ በህገወጥ መንገድ በወሃቢ ቡድን መወሰዱን” አውግዘዋል።5 ሰልፈኞቹ “መሪያችን ሃጅ ኡመር ኢድሪስ ናቸው”፣ “እስልምና አይሸጥም”፣ “መጅሊስ የሙስሊም እንጂ የውሃብያ ተቋም አይደለም” የሚሉ መፈክሮችን አሰምተዋል።6
ባለፈው ሳምንት በኦሮሚያ የተነሳው አለመግባባቶች ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ጋር ምንም ግንኙነት ባይኖረውም በመላ ሀገሪቱ በተለያዩ የኃይማኖት ተቋማት ውስጥ ያለው ውጥረት ትልቅ አዝማሚያ ያሳያል። የኢትዮጵያ የፖለቲካ ምህዳር እየተለወጠ በመጣ ቁጥር በኢትዮጵያ ውስጥ ተጨማሪ አለመግባባቶች የመፈጠር እድል አላቸው።
በተጨማሪም በኦሮሚያ ቤቶችን የማፍረስ እንቅስቃሴ ባለፈው ሳምንትም ቀጥሏል። የካቲት 14 ቀን የአዲሱ የሸገር ከተማ አካል በሆነው በለገጣፎ በአርባ-አራት ማዞረያ አበባ ልማት አካባቢ ቤታቸው እየፈረሰ ባለበት ወቅት የቤታቸው መፍረስን ነዋሪዎች ተቃውመዋል። ከቤት መፍረሱ ጋር በተያያዘ በተፈጠረ አለመግባባት የመንግስት የጸጥታ ኃይሎች ሁለት ሰላማዊ ሰዎችን ተኩሰው ሲገድሉ ቁጥራቸው በውል ያልታወቀ ሰዎች ቆስለዋል። የኦሮሚያ አዲሱ የሸገር ከተማ በአዲስ አበባ ዙሪያ በኦሮሚያ ልዩ ዞን ውስጥ የሚገኙ ከተሞችን፣ ወረዳዎችን እና አንዳንድ መንደሮችን በማዋሃድ በጥር 2015 ተመስርቷል።7 ከተማው ከተመሰረተ ጀምሮ የኦሮሚያ ክልላዊ መንግስት ‘ህገ-ወጥ ናቸው’ ያላቸውን ቤቶች እያፈረሰ ይገኛል።
በሶማሌ ክልል በሲቲ ዞን ኤረር ወረዳ አስቡሊ በተባለ ቦታ የአፋር ብሄር ታጣቂዎች ከሶማሌ ብሄር ታጣቂዎች ጋር ተዋግተዋል። በውጊያው ወደ 35 የሚጠጉ የሚሊሻዎች ህይወት ሲጠፋ በርካቶች ላይ ጉዳት ደርሷል። ከዚህ ውጊያ በስተጀርባ ያለው ምክንያት አልታወቅም። በአብዛኛው ጊዜ በእነዚህ ሁለት አካላት መካከል ውጊያዎች የሚነሱት በሶማሌ እና አፋር ክልል አዋሳኝ ላይ በሚገኙ አወዛጋቢ አካባቢዎች ምክንያት ነው (ለበለጠ መረጃ የኢፒኦን የአፋር–ሶማሌ ድንበር ግጭት ገፅ ይመልከቱ)።
በመጨረሻም የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በደቡብ ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ክልል (በደ/ብ/ብ/ሕ ክልል) በስድስት ዞኖች – በጋሞ፣ ወላይታ፣ ጎፋ፣ ጌዴኦ፣ ኮንሶ እና ደቡብ ኦሞ ዞኖች – እንዲሁም በአምስት ልዩ ወረዳዎች – ቡርጂ፣ አማሮ፣ ደራሼ፣ ባስኬቶእና አሌ – የተካሄደውን ህዝበ ውሳኔ ውጤት ይፋ ማድረግ ጀምሯል። ህዝበ ውሳኔው የተካሄደው ጥር 29 ሲሆን ውጤቱም ከላይ የተጠቀሱትን ዞኖች እና ልዩ ወረዳዎችን ያካተተ አዲስ ክልላዊ መንግስት ይቋቋም ወይስ አይቋቋም የሚለውን ይወስናል። በወላይታ ዞን በሚገኙ የተለያዩ የምርጫ ጣቢያዎች እንደ የመራጮች ምዝገባ፣ የመራጮች ቁጥር እና የተመዘገቡ መራጮች ቁጥር አለመጣጣም ወዘተ በመሳሰሉት የምርጫ ጉድለቶች ምክንያት የህዝበ ውሳኔው ውጤት ዘግይቷል።1 እስከ አሁን ለህዝብ ይፋ የተደረጉት ውጤቶቹ እንደሚያመለክቱት አብዛኛው መራጮች አዲስ ክልላዊ መንግስት መመስረቱን ይደግፋሉ።1