Skip to main content

ኢፒኦ ሳምንታዊ: ከየካቲት 18–24, 2015

Summary of political conflicts and events in Ethiopia, including Oromia protests and election outcomes.

9 March 2023

Also available in English

  • የፖለቲካ ግጭት ኩነቶች ብዛት: 1,202
  • በፖለቲካ ግጭቶች ምክንያት ሪፖርት የተደረጉ የሟቾች ቁጥር: 6,553
  • በሰላማዊ ሰዎች ላይ በተሰነዘሩ ጥቃቶች ምክንያት ሪፖርት የተደረጉ የሟቾች ቁጥር: 2,715
  • የፖለቲካ ግጭት ኩነቶች ብዛት: 4
  • በፖለቲካ ግጭቶች ምክንያት ሪፖርት የተደረጉ የሟቾች ቁጥር: 12
  • በሰላማዊ ሰዎች ላይ በተሰነዘሩ ጥቃቶች ምክንያት ሪፖርት የተደረጉ የሟቾች ቁጥር: 7

ኢትዮጵያን በተመለከተ በቁጥር የተደገፉ መረጃዎችን ከኢፒኦ የመረጃ መዝገብ እንዲሁም በዋናው የአክሌድ ኤክስፖርት መሳሪያ ውስጥ ማግኘት ይችላሉ።

የሁኔታዎች አጭር መግለጫ

በኢትዮጵያ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ግጭት የቀነሰ ቢሆንም ካለፉት ሳምንታት ጋር ሲነጻጸር ባለፈው ሳምንት ብዛት ያለው የሰልፍ እንቅስቃሴ ታይቷል። በኦሮሚያ ክልል አዲስ የተገለፀውን የአስተዳደር እርከን ማሻሻያዎች በመቃወም በርካታ የተቃውሞ ሰልፎች መኖራቸው የተገለፀ ሲሆን ሁለት የተቃውሞ ሰልፎች በኃይል ተበትነዋል። የኦሮሚያ ክልላዊ መንግስት ባለፈው ሳምንት የስድስት ከተሞችን መልሶ የማደራጀት እና የማቋቋም፣2 ለዘጠኝ ከተሞች የአስተዳደር እርከን መቀየሩን3 እና ምስራቅ ቦረና ዞን የሚባል አዲስ ዞን በክልሉ መቋቋሙን አስታውቋል።4

የካቲት 23 ቀን ኢትዮጵያውያን 127ኛውን የአድዋ ድል በዓልን – በየካቲት 1896 ዓ.ም. በዳግማዊ ምኒልክ መሪነት የኢትዮጵያ ጦር የጣሊያን ጦር ያሸነፈበት የድል በዓል – አክብረዋል። በአብዛኛው የሃገሪቱ ክፍል በዓሉ በሰላም ተከብሯል። ነገር ግን ልክ እንደ ባለፈው ዓመት በዋና ከተማዋ አዲስ አበባ በዓሉ ከሚከበርበት ስፍራ ጋር በተያያዘ ከፍተኛ ውጥረት ነግሶ ነበር (የባለፈው ዓመት አከባበር ላይ የበለጠ መረጃ ለማግኘት ኢፒኦ ሳምንታዊ: ከየካቲት 19, 2014 እስከ የካቲት 25, 2014 ይመልከቱ)። አብዛኛው የአዲስ አበባ ነዋሪ ቀኑን የዳግማዊ ምኒልክ ሃውልት ባለበት ፒያሳ በሚገኘው ዳግማዊ ምኒልክ አደባባይ ማክበርን ይመርጣሉ።5 በዚህ አመት መንግስት ያዘጋጀው የአድዋ ድል በዓል በመስቀል አደባባይ በኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት የቀረበ ወታደራዊ ትርኢትን ጨምሮ በተለያዩ መርሃ ግብሮች ተከብሯል።6 ዳግማዊ ምኒልክ የኢትዮጵያ ኢምፓየር ወደ ኦሮሚያ፣ ሶማሌ፣ አፋር፣ ጋምቤላ፣ ቤንሻንጉል/ጉሙዝ እና ደቡብ ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ክልል ማስፋፋታቸው በታሪክ ንጉሱን በሚመለከት የተለያያ አይነት አስተሳሰብ ሲኖር በኢትዮጵያ የንጉሱ ሐውልቶችና ሌሎች የአደባባይ መታሰቢያዎች ውዝግብ የሚያስነሱ ጉዳዮች ናቸው።7

በመስቀል አደባባይ በዓሉ እንዲከበር ለማድረግ በተደረገው ጥረት የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት፣ የፌዴራል ፖሊስ እና የአዲስ አበባ ፖሊሶች ጨምሮ የመንግስት የፀጥታ ኃይሎች ወደ ዳግማዊ ምኒልክ አደባባይ የሚወስዱትን መንገዶች በመዝጋት ህዝቡ ወደ አደባባዩ እንዳይገባ አግደዋል። በኋላም በዳግማዊ ምኒልክ አደባባይ የአድዋ ድል በዓልን ለማክበር በወጡ ሰዎች ላይ የፀጥታ ኃይሎች አስለቃሽ ጭስ እና የፕላስቲክ ጥይት ተኩሰዋል። አንዳንድ ዘገባዎች በዓሉን በሰላማዊ መንገድ በአደባባዩ ሲያከብሩ የነበሩ ሰዎችን ፖሊስ መበተን መጀመሩን ገልፀዋል።8 ሌሎች ዘገባዎች በህዝቡ ውስጥ የነበሩ ወጣቶች ድንጋይ የወረወሩ እና “ይህ ነው ንጉሳችን (ዳግማዊ ምኒልክ)” እያሉ እንደነበር አመላክተዋል።9 የሁለት ሰዎች ህይወት ማለፉ የተገለፀ ሲሆን 15 የቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ-ክርስቲያን ሰንበት ተማሪዎችን ጨምሮ ቁጥራቸው በውል ያልታወቁ ሰዎች ቆስለዋል። የሰንበት ተማሪዎቹ በአቅራቢያው በሚገኘው የቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ-ክርስቲያን ኃይማኖታዊ (ንግስ) በዓል ለማክበር ተሰብስበው ነበር።10 የፀጥታ ኃይሎች በቤተ-ክርስቲያኑ ውስጥ አስለቃሽ ጭስ ተኩሰዋል። አንዳንድ መረጃዎች እንደሚጠቁሙት ከሟቾቹ መካከል አንዱ በቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ-ክርስቲያን ውስጥ ኃይማኖታዊ ሥነ-ሥርዓቱን ሲያከብሩ በአስለቃሽ ጭስ ታፍነው ሕይወታቸው እንዳለፈ11 እና ሁለተኛው ደግሞ የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ አባል እና የሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት የሥነ-ዜጋ መምህር ሲሆኑ የፀጥታ ኃይሎች ወደ ህዝቡ ከተኮሱ በኋላ በተተኮሰ ጥይት ህይወታቸው አልፏል።

ይህ ክስተት በመንግስት እና በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ-ክርስቲያን (ኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ) መካከል ያለው ግንኙነት ከመቼውም ጊዜ ይበልጥ ዝቅ እንዲል አስተዋጽኦ አድርጓል።12 የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዴሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ (የኢፌዴሪ) መንግስት የኮሙዩኒኬሽን አገልግሎት በዳግማዊ ምኒልክ አደባባይ ለተፈጠረው ሁከት “በዓሉን ለማደናቀፍ እቅድ የያዙ አካላት”ን ተጠያቂ አድርጓል።13 በሌላ በኩል የኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት በቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ-ክርስቲያን ሁከተ ተፈጥሮ “የንግሥ በዓሉ መቋረጡ” መንግሥትን ተጠያቂ አድርጓል።14 አስለቃሽ ጭስ የተኮሱትን የፀጥታ ኃይሎች መንግስት ለህግ እንዲያቀርብ እና የታሰሩትን በ15 ቀናት ውስጥ ያለምንም ቅድመ ሁኔታ እንዲፈታ ሀገረ ስብከቱ ጠይቋል። ያለበለዚያ ቤተ-ክርስቲያን ተጨማሪ እርምጃዎችን እንደምትወስድ አስጠንቅቋል።15 እነዚህ ተጨማሪ እርምጃዎች ምን ሊሆኑ እንደሚችሉ ግልጽ አይደለም።

በሌላ በኩል በጋምቤላ ክልል የካቲት 18 ቀን ከደቡብ ሱዳን የመጡ የሙርሌ ብሔር ታጣቂዎች ድንበር ጥሰው በአኝዋክ ዞን ቦይ ቀበሌ ውስጥ በሰላማዊ ሰዎች ላይ ጥቃት በመሰንዘር አንድ ሰላማዊ ሰው ሲገድሉ ሌላ ሰላማዊ ሰው አቁስለዋል። ይህ ክስተተ በዲማ ወረዳ ባልታወቀ ቦታ በቀበሌ ታጣቂዎች እና በሙርሌ ታጣቂዎች መካከል ውጊያ አስከትሏል። የክልሉ መንግስት አምስት የሙርሌ ታጣቂዎች መገደላቸውን እና ሶስት ኤኬ (AK)-46 መሳሪያዎችን መያዙን ገልጿል።16

ባለፈው ሳምንት የትግራይ ክልል የሽግግር መንግስት የመመስረት ጉባኤ ከየካቲት 22 እስከ 23 በትግራይ ክልል መቀሌ ከተማ ተካሂዷል። በጉባኤው የትግራይ ህዝብ፣ የትግራይ ታጣቂ ኃይሎች፣ የሲቪክ ማህበራት እና የኃይማኖት ተቋማት ተወካዮች ተገኝተዋል። ሆኖም የገዢው ብልፅግና ፓርቲ ተወካዮችን ጨምሮ አብዛኞቹ ተቃዋሚ ፓርቲዎች አልተገኙም። “በጊዜያዊ አስተዳደሩ ማዋቀር ሕጋዊነት፣ ፍትሓዊነትና አሳታፊነት ላይ ጥያቄዎች በማንሳት” ተቃዋሚ ፓርቲዎች ራሳቸው ከሂደቱ በማግለል በጉባኤው ሳይሳተፉ ቀርተዋል።17 የጉባኤው ተሳታፊዎች የትግራይ ክልል ሽግግር መንግስትን ለመመስረት በመስማማት ጉባኤው ተጠናቋል። የሽግግር መንግሥቱ 28 አባላት የሚኖሩት ሲሆን አንድ ፕሬዚዳንት እና ሁለት ምክትል ፕሬዚዳንቶች ይኖሩታል። ከእነዚህ ውስጥ 50% የሚሆኑት ከትግራይ ህዝብ ነፃነት ግንባር (ትህነግ/ህወሓት)፣ 29% ከትግራይ ኃይሎች፣ ቀሪው 21% ከተቃዋሚ ፓርቲዎች እንደሚሆኑ ተነግሯል።18 በጥቅምት 23 ቀን በተፈረመው የሰላም ስምምነት መሰረት ትህነግ/ህወሓት እና የኢትዮጵያ መንግስት ክልላዊ ምርጫ እስኪደረግ ድረስ “አካታች” ጊዜያዊ የሽግግር መንግሥት ለመመስረት ተስማምተዋል።19 የሽግግር መንግስቱ ከስድስት ወር እስከ አንድ አመት የሚቆይ ሲሆን በዚህ ጊዜ ውስጥ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ (ምርጫ ቦርድ) የትግራይ ክልል መንግስትን ለመመስረት የሚያስችል ክልላዊ ምርጫ ያዘጋጃል። የሽግግር መንግስቱ የሚመሰረተው የትህነግ/ህወሓት ተወካዮች እና የፌዴራል መንግስት ስብሰባ አድርገው አደረጃጀቱን ሲያፀድቁ ነው።20

በመጨረሻም የካቲት 22 ቀን ምርጫ ቦርድ በወላይታ ዞን የተለያዩ የምርጫ ምዝገባና የምርጫ ጉድለቶች በመገኘታቸው ምክንያት የተካሄደው የሕዝበ ውሳኔ እንዲሰረዝ ወስኗል።21 በጥር 29 ቀን ሕዝበ ውሳኔ በደቡብ ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ክልል (በደ/ብ/ብ/ሕ ክልል) በስድስት ዞኖች – በጋሞ፣ ወላይታ፣ ጎፋ፣ ጌዴኦ፣ ኮንሶ እና ደቡብ ኦሞ ዞኖች – እንዲሁም በአምስት ልዩ ወረዳዎች – ቡርጂ፣ አማሮ፣ ደራሼ፣ ባስኬቶእና አሌ – ተካሂዷል። ሕዝበ ውሳኔው የተካሄደው ከላይ የተጠቀሱትን ዞኖች እና ልዩ ወረዳዎችን በማካተት አዲስ ክልላዊ መንግስት እንዲቋቋም ለመወሰን ነው። ምርጫ ቦርድ ሁሉም ዞኖችና ልዩ ወረዳዎች የሚገኙ የ81 የምርጫ ጣቢያዎችን ውጤት ሰርዟል። ነገር ግን ይህ ስረዛ አጠቃላይ ውጤቱን ስለማይነካ (ስለማይለውጥ) ምርጫ ቦርድ በተቀሩት ዞኖች እና ልዩ ወረዳዎች የሕዝበ ውሳኔውን ውጤት ይፋ አድርጓል። አብዛኛው መራጮች አዲስ ክልል መመስረቱን ደግፈዋል።22

Footnotes

  1. 2

    የኦሮሚያ ብሮድካስቲንግ ኔትወርክ፣ ‘የኦሮሚያ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት ምክር ቤት ባካሄደው መደበኛ ጉባኤው የተለያዩ ውሳኔዎችን አሳልፏል፣’ የካቲት 20, 2015

  2. 3

    ኦቢኤን፣ ‘የኦሮሚያ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት ምክር ቤት ባካሄደው መደበኛ ጉባኤው የተለያዩ ውሳኔዎችን አሳልፏል፣’ የካቲት 20, 2015

  3. 4

    ኦቢኤን፣ ‘የኦሮሚያ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት ምክር ቤት ባካሄደው መደበኛ ጉባኤው የተለያዩ ውሳኔዎችን አሳልፏል፣’ የካቲት 20, 2015

  4. 5

    ፌስቡክ @ክርስትያን ታደለ ፀጋዬ፣ ‘የ127ኛ ዓመት የዓድዋ በዓል አከባበርን አስመልክቶ ከአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) የተሰጠ መግለጫ፣’ የካቲት 23, 2015

  5. 6

    የኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን፣ ‘የ127ኛው የዓድዋ ድል በዓል የሰልፍ ትርዒቶች፣’ የካቲት 23, 2015

  6. 7

    አወል አሎ፣ ‘‘ትልቅ ፀረ-ቅኝ አገዛዝ ድል ኢትዮጵያን እንዴት እንደከፋፈላት፣’ አልጀዚራ፣ የካቲት 22, 2011

  7. 8

    የኢትዮጵያ ሚዲያ ስርቪስ፣ ‘ኢኤምኤስ መረጃ ሀሙስ የካቲት 23፣ 2015፣’ የካቲት 23፣ 2015

  8. 9

    ቲክቫህ-ኢትዮጵያ፣ ‘የዓድዋ በዓል በአዲስ አበባ?’ የካቲት 23, 2015

  9. 10

    የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ-ክርስትያን መገናኛ ብዙኀን አገልግሎት ሥርጭት ድርጅት፣ ‘በመናገሻ ገነተ ጽጌ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን ላይ በመንግሥት የጸጥታ ኃይሎች አማካኝነት የተፈጸመውን ሕገ ወጥ ድርጊት አስመልክቶ ከአዲስ አበባ ሀገረ ሰብከት የተሰጠ መግለጫ፣’ የካቲት 24, 2015

  10. 11

    የኢኦተቤ መገናኛ ብዙኀን አገልግሎት ሥርጭት ድርጅት፣ ‘በመናገሻ ገነተ ጽጌ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን ላይ በመንግሥት የጸጥታ ኃይሎች አማካኝነት የተፈጸመውን ሕገ ወጥ ድርጊት አስመልክቶ ከአዲስ አበባ ሀገረ ሰብከት የተሰጠ መግለጫ፣’ የካቲት 24, 2015

  11. 12

    በየካቲት 2015 በኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ ውስጥ በተከሰተው ግጭት የተነሳ በመንግስት እና በኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ መካከል ከፍተኛ ውጥረት ነበር።

  12. 13

    የኢፌዴሪ መንግስት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት፣ ‘127ኛው የአድዋ ድል በዓል በመላ ሀገሪቱ በወጣለት ፕሮግራም መሠረት ተከብሯል። ለዚህ ስኬት አስተዋጽዖ ያደረጉትን አካላት ሁሉ መንግሥት ያመሰግናል፣’ የካቲት 23, 2015

  13. 14

    የኢኦተቤ መገናኛ ብዙኀን አገልግሎት ሥርጭት ድርጅት፣ ‘በመናገሻ ገነተ ጽጌ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን ላይ በመንግሥት የጸጥታ ኃይሎች አማካኝነት የተፈጸመውን ሕገ ወጥ ድርጊት አስመልክቶ ከአዲስ አበባ ሀገረ ሰብከት የተሰጠ መግለጫ፣’ የካቲት 24, 2015

  14. 15

    የኢኦተቤ መገናኛ ብዙኀን አገልግሎት ሥርጭት ድርጅት፣ ‘በመናገሻ ገነተ ጽጌ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን ላይ በመንግሥት የጸጥታ ኃይሎች አማካኝነት የተፈጸመውን ሕገ ወጥ ድርጊት አስመልክቶ ከአዲስ አበባ ሀገረ ሰብከት የተሰጠ መግለጫ፣’ የካቲት 24, 2015

  15. 16

    የጋምቤላ ክልል መንግስት ፕሬስ ሴክሬታሪያት ጽህፈት ቤት፣ ‘ከደቡብ ሱዳን የተሻገሩ የሙርሌ ጎሳ ታጣቂዎች በጋምቤላ ክልል ዲማ ወረዳ ቦይ ቀበሌ አንድ ሰው ገድለው አንድ ሰው ማቁሰላቸውን የክልሉ ሰላምና ፀጥታ አስተዳደር ቢሮ አስታወቀ፣’ የካቲት 19, 2015

  16. 17

    ዶይቸ ቬለ አማርኛ፣ የካቲት 22, 2015

  17. 18

    ዮሐንስ አንበርብር፣ ‘በትግራይ 28 አባላት የሚኖሩት የሽግግር መንግሥት እንዲመሠረት ተወሰነ፣’ የኢትዮጵያ ሪፖርተር፣ የካቲት 26, 2015

  18. 19

    የኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር፣ ‘በኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዲሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ መንግስት እና በትግራይ ህዝብ ነፃነት ግንባር (ትህነግ/ህወሓት) መካከል የተደረገ ለዘለቄታዊ ሰላም ቋሚ የተኩስ አቁም ስምምነት፣’ ጥቅምት 25, 2015

  19. 20

    ዮሐንስ አንበርብር፣ ‘በትግራይ 28 አባላት የሚኖሩት የሽግግር መንግሥት እንዲመሠረት ተወሰነ፣’ የኢትዮጵያ ሪፖርተር፣ የካቲት 26, 2015

  20. 21

    የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ፣ ‘የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በደ/ብ/ብ/ሕ ክልላዊ መንግስት ሥር በሚገኙ ስድስት ዞኖች እና አምስት ልዮ ወረዳዎች ላይ ያካሄደው የሕዝበ ውሳኔ አፈፃፀም እና ውጤት አስመልክቶ የተሰጠ መግለጫ፣’ የካቲት 22, 2015

  21. 22

    የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ፣ ‘የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በደ/ብ/ብ/ሕ ክልላዊ መንግስት ሥር በሚገኙ ስድስት ዞኖች እና አምስት ልዮ ወረዳዎች ላይ ያካሄደው የሕዝበ ውሳኔ አፈፃፀም እና ውጤት አስመልክቶ የተሰጠ መግለጫ፣’ የካቲት 22, 2015

Country
Ethiopia
Region
Africa
Share on

Related content