ኢፒኦ ሳምንታዊ: ከየካቲት 4–10, 2015
ሳምንታዊ ዘገባ ይወስዳል: በውስጥ እና ውጪ አካባቢዎች የተከሰቱ ግጭቶች እና ሊኒስትር ያለሙዚክ የፖለቲካ ልዩ ወቅቱን ይዋሇዋል።
Also available in English
- የፖለቲካ ግጭት ኩነቶች ብዛት: 1,226
- በፖለቲካ ግጭቶች ምክንያት ሪፖርት የተደረጉ የሟቾች ቁጥር: 6,475
- በሰላማዊ ሰዎች ላይ በተሰነዘሩ ጥቃቶች ምክንያት ሪፖርት የተደረጉ የሟቾች ቁጥር: 2,624
- የፖለቲካ ግጭት ኩነቶች ብዛት: 3
- በፖለቲካ ግጭቶች ምክንያት ሪፖርት የተደረጉ የሟቾች ቁጥር: 0
- በሰላማዊ ሰዎች ላይ በተሰነዘሩ ጥቃቶች ምክንያት ሪፖርት የተደረጉ የሟቾች ቁጥር: 0
ኢትዮጵያን በተመለከተ በቁጥር የተደገፉ መረጃዎችን ከኢፒኦ የመረጃ መዝገብ እንዲሁም በዋናው የአክሌድ ኤክስፖርት መሳሪያ ውስጥ ማግኘት ይችላሉ።

የሁኔታዎች አጭር መግለጫ
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን (ኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ) ሲኖዶስ የተፈጠረው ችግር “በቤተ-ክርስቲያኒቱ ቀኖና መሠረት” መፈታቱን የሚያመላክት መግለጫ የካቲት 8 ቀን ማውጣቱን ተከትሎ ከኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ ጋር ተያይዞ የነበረው የፖለቲካ ውጥረት ባለፈው ሳምንት ረግቧል።2 የኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ ሲኖዶስ እና በአቡነ ሳዊሮስ የሚመራው ቡድን የቤተ-ክርስቲያኒቱን አገልግሎት በአፋን ኦሮሞ (በኦሮምኛ ቋንቋ) ማጠናከር እና የሦስቱን ሊቀነ ጳጳሳት እና 25 አባቶችን ወደ ቀድሞ ቦታቸው መመለስን ጨምሮ በ10 ጉዳዮች ላይ ተስማምተዋል።3 ሁለቱ ወገኖች ከጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ እና ከሽማግሌዎች ጋር ከተመካከሩ በኃላ ከስምምነት ላይ ደርሰዋል።4 አለመግባባቱ የጀመረው ጥር 14 ቀን የደቡብ ምዕራብ ሸዋ ሊቀ ጳጳስ አቡነ ሳዊሮስ ከሌሎች ሁለት ሊቃነ ጳጳሳት ጋር በመሆን በደቡብ ምዕራብ ሸዋ ዞን ወሊሶ ከተማ በሚገኘው ሐሮ በዓለ ወልድ ቤተ-ክርስቲያን 26 ጳጳሳትን ሾመው “የኦሮሚያ እና የብሔር ብሔረሰቦች ቅዱስ ሲኖዶስ” መቋቋሙን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ሲኖዶስ ሳያውቅ ይፋ ካደረጉ በኃላ ነው።5 ይህ አለመግባባት ወደ ግጭት የተሸጋገረው ጥር 27 ቀን ‘የኦሮሚያ እና የብሔር ብሔረሰቦች ቅዱስ ሲኖዶስ’ በተለያዩ የኦሮሚያ ክልል አካባቢዎች ኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ ንብረት የሆኑ አብያተ-ክርስቲያናትን መረከብ ሲጀምር ነበር (ለበለጠ መረጃ ኢፒኦ ሳምንታዊ: ከጥር 27–የካቲት 3, 2015 እና ኢፒኦ ሳምንታዊ: ከጥር 20-26, 2015 ይመልከቱ)።
ባለፈው ሳምንት የኦርቶዶክስ ተዋህዶ አማኞች እና ጋዜጠኞች እስራት በሀገሪቱ ቀጥሏል።1 የካቲት 8, 2015 ዓ.ም የኦሮሚያ ፖሊስ በኦሮሚያ ክልል በሽገር ከተማ ወለቴ ቁጥራቸው በውል ያልታወቀ በአብዛኛው አማራ እና ጉራጌ የሆኑ የኦርቶዶክስ ክርስትያኖችን በቁጥጥር ስር አውሏል።
በኦሮሚያ ክልል በኦሮሞ ነጻነት ግንባር (ኦነግ)-ሸኔ (የኦሮሞ ነጻነት ሠራዊት በመባልም የሚታወቀው) በሰላማዊ ሰዎች ላይ ያደረሰው ሁለት ጥቃቶች ተመዝግበዋል (ከዚህ በታች ያለውን ካርታ ይመልከቱ)። የኦነግ-ሸኔ አባላት ባለፈው ሳምንት ከምስራቅ ሸዋ ዞን አዳማ ከተማ ወደ አርሲ ዞን አቦምሳ እና ከአቦምሳ ወደ አልታወቀ ቦታ ሲጓዙ የነበሩ ሰላማዊ ሰዎችን በአቦምሳ አቅራቢያ በሚገኝ አካባቢ ተሽከርካሪዎቻቸውን በማስቆም ቁጥራቸው በውል ያልተገለጸ ሰላማዊ ሰዎችን አፍነው ወስደዋል። ባለፈው ሳምንት በመንግስት ታጣቂዎችም በርካታ ክስተቶች መከሰታቸው ተዘግቧል። በምዕራብ ሸዋ ዞን በኢፋታ ወረዳ ጂርማ ቆጴሳ ቀበሌ የቀበሌ ታጣቂዎች ከኦነግ-ሸኔ ጋር ተባብረዋል በሚል የሰላማዊ ሰዎች ቤቶችን አቃጥለዋል። የኦሮሚያ ክልል ልዩ ኃይል አባላት እንደሆኑ የተገመቱ የመንግስት የጸጥታ ኃይሎች በአርሲ ዞን በጀጁ ወረዳ በአላጋ ዱሬቲ ቀበሌ በርካታ ወጣቶችን ኦነግ-ሸኔን ይደግፋሉ በሚል በቁጥጥር ስር አውለዋል።

በኦነግ-ሸኔ እና በመንግስት የጸጥታ ኃይሎች መካከል ባለው ውጊያ ምክንያት የኦሮሚያ ክልል ባለፉት አራት ወራት ውስጥ በሀገሪቱ ካሉ አካባቢዎች እጅግ በጣም ያልተረጋጋ ክልል ሆኖ ቆይቷል። ጥር 10 ቀን የኦሮሚያ ክልል ፕሬዝደንት በአዳማ ከተማ የኦሮሚያ ክልል ምክር ቤት (ጨፌ ኦሮሚያ) ባካሄደው አራተኛ መደበኛ ስብሰባ ላይ “ኦነግ-ሸኔ ያለውን ግጭት በሰላማዊ መንገድ እንዲያቆምና ድርድር እንዲጀምር” ባልተጠበቀ መልኩ ጥሪ አቅርበዋል።7 ከዚህ ቀደም መንግስት ከኦነግ-ሸኔ ጋር ለመደራደር ፈቃደኛ አለመሆኑን ተናግሮ ነበር (ለበለጠ መረጃ ኢፒኦ ከሕዳር 22 እስከ ታህሳስ 22, 2015፡ በኦሮሚያ ክልል ግጭት መስፋፋትን ይመልከቱ)። የኦሮሞ ነጻነት ሠራዊት የሰላም ጥሪውን ቢቀበልም ድርድሩን ለመጀመር ቅድመ ሁኔታዎችን ዘርዝሯል፣ ከእነዚህም መካከል ድርድሩ በአለም አቀፍ አካላት እንዲመራ እና ዋስትና እንዲሰጥ እና ድርድሩ ከኦሮሚያ ክልላዊ መንግስት ጋር ሳይሆን በቀጥታ ከፌዴራል መንግስት ጋር እንዲደረግ ጠይቋል።8 የሰላም ድርድር ጥሪው ከመደረጉ ጥቂት ቀናት በፊት አንዳንድ ተደማጭነት ያላቸው የኦሮሞ ተወላጅ ዲያስፖራ ድርጅቶች የሰላም ጥረት እንደሚደግፉ ጠቁመው መንግስት ድርድር እንዲቀጥል ጠይቀው ነበር።9
በደቡብ ብሔር ብሔረሰቦችና ህዝቦች ክልል የካቲት 8 ቀን የወልቂጤ ከተማ ነዋሪዎች በጉራጌ ዞን ወልቂጤ ከተማ ውሃና ሳኒቴሽን ፅህፈት ቤት ደጃፍ ላይ በመሰባሰብ በአንዳንድ አካባቢዎች ከአንድ ወር በላይ የተከስተውን የመጠጥ ውሃ ችግር በመቃወም ሰላማዊ ሰልፍ ወጥተዋል። ሰልፈኞቹ መንገድ ዘግተው በህንፃው ላይ ድንጋይ ወርውረዋል። የክልሉ ልዩ ኃይል በሰልፈኞቹ ላይ ጥይት በመተኮሱ ቢያንስ ሦስት ሰዎች መሞታቸው እና 30 ሰዎች መቁሰላቸው ታውቋል። ከዚያን ጊዜ ጀምሮ የወልቂጤ ከተማ ነዋሪዎች ሱቆችን በመዝጋት “ሰላማዊ ሰዎችን የገደሉ የጸጥታ ኃይሎች ለፍርድ እስኪቀርቡ ድረስ” ከቤት ባለመውጣት ተቃውሟቸውን እያሰሙ ይገኛሉ።10 ይህ በቤት ውስጥ የመቆየት ተቃውሞ ለስድስተኛ ቀን የካቲት 13 ቀን ቀጥሏል። ይህ በእንዲህ እንዳለ የመንግስት የጸጥታ ኃይሎች “ነዋሪውን በማስፈራራት ሱቆቻቸውን እንዲከፍቱ” በከተማው ውስጥ ሰላማዊ ሰዎችን ማሰር መቀጠላቸው መረጃዎች ያመለክታሉ።11
በዋና ከተማዋ አዲስ አበባም ሌላ ሰልፍ መደረጉ ተዘግቧል። የካቲት 8 ቀን በከተማዋ እና በኦሮሚያ ክልል ሱሉልታ አዋሳኝ አካባቢ በፈረንሣይ ጉራራ ኪዳነ ምሕረት ቤተ ክርስቲያን ዙሪያ በመንግሥት ሊደረግ የታስበውን ቤት የማፍረስ እርምጃ ለማውገዝ ወጣቶች የተቃውሞ ሰልፍ አድርገዋል። የፌዴራል ፖሊስ እና የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት አባላት አስለቃሽ ጭስ በመተኮስ ቁጥራቸው በውል የማይታወቁ ሰልፈኞችን በቁጥጥር ስር አውለዋል። መንግሥት እነዚህን ቤቶች “በሕገወጥ መንገድ” የተገነቡ ቤቶች ናቸው በማለት የለያቸው ናቸው።12
በአማራ ክልል በኦሮሚያ ልዩ ዞን በጅልዬ ጥሙጋ ወረዳ በወሰን ኩርኩር ቀበሌ የአማራ ክልል ልዩ ኃይል እና የአማራ ብሔር ታጣቂዎች በርካታ የሰላማዊ ሰዎች ቤቶችን፣ ጤና ጣቢያዎችን እና መስጊዶችን አቃጥለዋል። በዚህም ምክንያት በርካታ ነዋሪዎች ቤታቸውን ለቀው ለመሰደድ ተገደዋል። ይህ አካባቢ በጥር ወር ውስጥ የአማራ ክልል ልዩ ኃይል፣ የአማራ ብሔር ታጣቂዎች፣ የኦሮሚያ ብሔር ታጣቂዎች እና ኦነግ-ሸኔን ያሳተፈ የግጭት ማዕከል ነበር (ለበለጠ መረጃ የኢፒኦ ሳምንታዊ: ከጥር 13-19, 2015 ይመልከቱ)።
በተጨማሪም ከአማራ ክልል ወደ አዲስ አበባ የሚወስደው መንገድ በኦሮሚያ ክልል ሰሜን ሸዋ ዞን ጎሃ ጽዮን ኬላ ላይ በኦሮሚያ ክልል ልዩ ኃይሎች ለቀናት ተዘግቷል።13 የመንገዱ መዘጋት በሰላማዊ ሰዎች ላይ ከፍተኛ መስተጓጓል ያደረሰ ሲሆን አብዛኞው የአማራ ክልል መታወቂያ የያዙ ሰዎች ወደ አዲስ አበባ እንዳይገቡ ተደርጓል። በዚህ ምክንያት መንገዱ በቅርቡ ይከፈታል በሚል በመቶዎች የሚቆጠሩ ሰላማዊ ሰዎች በተለያዩ አካባቢዎች፣ መስጊዶች እና ቤተ-ክርስትያን ጨምሮ በአቅራቢያ ባሉ የአማራ ከተሞች ለተከታታይ ቀናት ለመቆየት ተገደዋል። መንገዱ ከየካቲት 2 ጀምሮ ለተከታታይ ቀናት ተዘግቷል ተብሏል። የአማራ ክልል ኮሙዩኒኬሽን ፅህፈት ቤት ኃላፊ እንደገለፁት መንገዱ ለምን ይህን ያህል ጊዜ እንደተዘጋ ግልፅ አይደለም። ነገር ግን የካቲት 5 ቀን በኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ ሲኖዶስ የተጠራው ነገር ግን የካቲት 3 ቀን የተራዘመውን ሀገር አቀፍ ሰላማዊ ሰልፍ በመፍራት መንግስት ኬላዎችን በጥብቅ ለመቆጣጠር እና መንገዱን ለአንድ ቀን ለመዝጋት ተስማምተው እንደነበር አምነዋል።14 ይህ መንገድ ባለፉት ጥቂት ወራት ውስጥ ብዙ ጊዜ ተዘግቷል።
Footnotes
- 1
አዲስ ማለዳ፣ ‘በቤተክርስቲያን ወቅታዊ ጉዳይ ላይ ከመንግሥት ጋር ስምነነት ከተደረገ በኋላም ውዝግቡ ቀጥሏል፣’ የካቲት 7, 2015
- 2
የኢኦተቤ መገናኛ ብዙኀን አገልግሎት ሥርጭት ድርጅት፣ ‘የቅዱስ ሲኖዶስ መግለጫ ሙሉ ቃል፣’ የካቲት 8, 2015
- 3
- 4
- 5
- 7
ኦቢኤን አፋን ኦሮሞ፣ ‘የኦሮሚያ ክልል ፕሬዝዳንት አቶ ሽመልስ አብዲሳ ለኦነግ-ሸኔ የእርቅ ጥሪ አቀረቡ፣’ የካቲት 10, 2015
- 8
የኦሮሞ ነጻነት ሠራዊት፣ ‘የኦሮሚያ ክልል መንግስት ያቀረበውን የሰላም ጥሪ አስመልክቶ፣’ የካቲት 11, 2015
- 9
- 10
ዶይቸ ቬለ አማርኛ፣ ‘የዓለም ዜና፤ የካቲት 13 ቀን 2015 ዓ.ም ሰኞ፣’ የካቲት 13, 2015
- 11
ዶይቸ ቬለ አማርኛ፣ ‘የዓለም ዜና፤ የካቲት 13 ቀን 2015 ዓ.ም ሰኞ፣’ የካቲት 13, 2015
- 12
ዋዜማ ሬዲዮ፣ ‘ለቸኮለ ማለዳ! ሐሙስ የካቲት 9/2015 ዓ.ም የዋዜማ ዐበይት ዜናዎች፣’ የካቲት 9, 2015
- 13
- 14