Skip to main content

ኢፒኦ ሳምንታዊ: መጋቢት 16-22, 2015

Analysis of recent political conflicts and events in Ethiopia.

6 April 2023

Also available in English

  • የፖለቲካ ግጭት ኩነቶች ብዛት: 1,153
  • በፖለቲካ ግጭቶች ምክንያት ሪፖርት የተደረጉ የሟቾች ቁጥር: 6,238
  • በሰላማዊ ሰዎች ላይ በተሰነዘሩ ጥቃቶች ምክንያት ሪፖርት የተደረጉ የሟቾች ቁጥር: 2,634
  • የፖለቲካ ግጭት ኩነቶች ብዛት: 9
  • በፖለቲካ ግጭቶች ምክንያት ሪፖርት የተደረጉ የሟቾች ቁጥር: 6
  • በሰላማዊ ሰዎች ላይ በተሰነዘሩ ጥቃቶች ምክንያት ሪፖርት የተደረጉ የሟቾች ቁጥር: 3

ኢትዮጵያን በተመለከተ በቁጥር የተደገፉ መረጃዎችን ከኢፒኦ የመረጃ መዝገብ እንዲሁም በዋናው የአክሌድ ኤክስፖርት መሳሪያ ውስጥ ማግኘት ይችላሉ።

የሁኔታዎች አጭር መግለጫ

ባለፈው ሳምንት አክሌድ በኢትዮጵያ ውስጥ ዘጠኝ የፖለቲካ ግጭት ኩነቶች የመዘገበ ሲሆን ከእነዚህ ውስጥ ስምንቱ በኦሮሚያ ክልል ተመዝግበዋል (ከዚህ በታች ያለውን ካርታ ይመልከቱ)። በኦሮሚያ የተመዘገቡት የፖለቲካ ግጭት ኩነቶች ሦስት የጦርነት ኩነቶች እና አምስት በሰላማዊ ሰዎች ላይ የተፈጸሙ ጥቃት ኩነቶች ናቸው። አብዛኛዎቹ እነዚህ ክስተቶች በምስራቅ ሸዋ እና በሰሜን ሸዋ ዞኖች የተከሰቱ ናቸው።

መጋቢት 16 ቀን በሰሜን ሸዋ ዞን ደራ ወረዳ በባቡ ድሬ፣ ማንቃት፣ ጅሩ፣ አዳአ መልኬ፣ ከሩ ሲባ፣ ሀርቡ ድሬ እና ሀሙማ ገንዶ ቀበሌዎች የኦሮሞ ነጻነት ግንባር (ኦነግ)-ሸኔ የሰላማዊ ሰዎችን ቤቶች ካወደመ በኃላ ከ100 በላይ ሰላማዊ ሰዎችን አፍኖ ወስዷል።2 ከሁለት ቀናት በኋላ መጋቢት 18 ቀን ቡድኑ ሌሎች ሶስት ሰላማዊ ሰዎችን በወረዳው አፍኖ ወስዷል። እነዚህ ታፈነው የተወሰዱ ሶስት ሰላማዊ ሰዎች በተመሳሳይ ቀን በደራ ወረዳ በጅማ በር አካባቢ የመንግስት ኃይሎች ከኦነግ-ሸኔ አባላት ጋር ከተዋጉ በኃላ ተለቀዋል። በሚቀጥለው ቀን በወረዳው ውስጥ ባልታወቁ ቦታዎች ውጊያው ቀጥሏል። በእነዚህ ውጊያዎች ምክንያት ጉዳት መድረሱ እስካሁን የታወቀ ነገር የለም።

በምስራቅ ሸዋ ዞን ፈንታሌ ወረዳ አርዳ ጅላ አካባቢ መጋቢት 16 ቀን የፀጥታ ኃይሎች የወቅቱን የከረዩ አባ ገዳ መሪን (የከረዩ ጎሳ ባህላዊ መሪን) ጨምሮ 18 ሽማግሌዎችን ባልታወቀ ምክንያት ደብድበዋል። ከሁለት ቀን በኋላ የከረዩ አባ ገዳ መሪ በድብደባው በደረሰባቸው ጉዳት ህይወታቸው አልፏል።3 ጥቃቱ ከመፈጸሙ ሁለት ቀናት ቀደም ብሎ መጋቢት 14 ቀን የመንግስት ኃይሎች እና ኦነግ-ሸኔ በምስራቅ ሸዋ ዞን ቦሰት እና መርቲ ወረዳዎች አዋሳኝ ላይ በሚገኘው ቦሌ አካባቢ ተዋግተዋል። ሁለቱ ቡድኖች መጋቢት 17 ቀን በፈንታሌ ወረዳ ተዋግተው ነበር። ከአንድ አመት በፊት ህዳር 22, 2014 በፈንታሌ ወረዳ የፀጥታ ኃይሎች 14 የከረዩ አባ ገዳ አባላትን በጥይት ተኩስው ገድለው ነበር። ይህ ከህግ አግባብ ውጪ የተፈፀመ ግድያ ከመፈፀሙ አንድ ቀን ቀደም ብሎ ማንነቱ ያልታወቀ ታጣቂ ቡድን በፈንታሌ ወረዳ ሃሮ ቀርሳ ቀበሌ ኢፍቱ በተባለ ሥፍራ በፀጥታ ኃይሎች ላይ የደፈጣ ጥቃት ያደረሰ ሲሆን በዚህም 11 የኦሮሚያ ክልል ልዩ ኃይል አባላት ሲገደሉ በትንሹ ሰባት የኦሮሚያ ፖሊስ አባላት ቆስለዋል። የፀጥታ ኃይሎቹ ጥቃት የደረሰባቸ በፈንታሌ ወረዳ “የፀጥታ ስምሪት” አድርገው ወደ መተሃራ በመመለስ ላይ በነበሩበት ወቅት ነው።4

በተጨማሪም መጋቢት 21 ቀን ማንነታቸው ያልታወቁ ታጣቂዎች በነቀምት የሚገኘውን የገዥው የብልጽግና ፓርቲ ፅሕፈት ቤት ኃላፊ ወደ ቢሮአቸው እያመሩ ባለበት ወቅት በጥይት ተኩሰው ገድለዋል። በክልሉ በአብዛኛው በምዕራብ ኦሮሚያ የመንግስት ባለስልጣናትን እና የመንግስት ደጋፊዎችን መግደል የተለመደ ነው። ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ ስልጣን ከያዙበት ጊዜ አንስቶ ማለትም ከመጋቢት 2010 ጀምሮ እስከ መጋቢት 2015 ድረስ አክሌድ በኦሮሚያ የመንግስት ባለስልጣናት ላይ ያነጣጠሩ 29 የጥቃት ኩነቶችን  ከ66 ሪፖርት ከተደረጉ የሟቾች ቁጥር ጋር  መዝግቧል። በርካታ ከንቲባዎች፣ አስተዳዳሪዎች፣ ምክትል አስተዳዳሪዎች እና የመንግስት የተለያዩ ኃላፊዎች አባ ቶርቤ ከሚባለው የኦነግ-ሸኔ የከተማ ቡድን ጋር ግንኙነት አንዳላቸው የሚገመት ማንነታቸው ባልታወቁ ታጣቂዎች ተገድለዋል።5

በኦሮሚያ ክልል በቅርቡ በተቋቋመው ሸገር ከተማ – የቀድሞ የፊንፊኔ ልዩ ዞን – ከመኖሪያ ቤቶች መፍረስ ጋር ተያይዞ የሚነሳ ግጭት ቀጥሏል። ባለፈው ሳምንት በለገጣፎ አካባቢ ቤታቸውን ለማፍረስ የተላኩትን አፍራሽ ግብረ-ኃይልን ለማስቆም የሞከሩ ግለሰቦች የኦሮሚያ ክልል ልዩ ኃይል አባላት እንደሆኑ በተገመቱ የፀጥታ ኃይሎች ተደብድበዋል። የፀጥታ ኃይሎች ተኩስም የከፈቱ ሲሆን ቢያንስ አንዲት ሴት አቁስለዋል።

ሶማሌ ክልል መጋቢት 17 እና 18 በሲቲ ዞን አይሻ ወረዳ የአይሻ ከተማ ነዋሪዎች የኢትዮ-ጅቡቲ አውራ ጎዳናን እና የባቡር መንገድ በመዝጋት የሶማሌ ተወላጆች በአፋር ታጣቂዎች መፈናቀላቸውን ተቃውመዋል። ሰልፈኞቹ መንግስት የተፈናቀሉትን ወደ ቀድሞ መኖሪያቸው እንዲመልስ ጠይቀዋል። የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት አዛዦች ከማህበረሰብ ሽማግሌዎች ጋር ተወያይተው የተዘጋውን አውራ ጎዳና እንዲከፍቱ አሳምነዋል። ሆኖም አንዳንድ ተቃዋሚዎች መንግስት መጀመሪያ “ሶማሌዎችን ወደ መሬታቸው እንዲመልስ” በመጠየቅ አውራ ጎዳናውን ለመክፈት ፈቃደኛ አልሆኑም።6 በዚህ ምክንያት መጋቢት 18 ቀን የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት አባላት የተዘጋውን መንገድ በኃይል ለመክፈት ሲሞክሩ ሦስት ሰላማዊ ሰዎችን ተኩሰው ገድለው ስድስት ሰዎችን አቁስለዋል።

ከሰሜን ኢትዮጵያ ግጭት ጋር በተያያዘ በርካታ አዳዲስ ክስተቶች ባለፈው ሳምንት ተዘግበዋል። መጋቢት 19 ቀን የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት በአማራ ክልል ዋግ ኸምራ ዞን የአበርገሌ ወረዳ የአስተዳደር ማዕከል የሆነችውን ንየር አኩ ከተማን ተቆጣጥሯል። ከሐምሌ 2013 ጀምሮ የአበርገሌ ወረዳ አንዳንድ ቦታዎች በትግራይ ህዝብ ነፃነት ግንባር (ትህነግ/ህወሓት) ኃይሎች እና በአገው ዲሞክራሲ ንቅናቄ ታጣቂዎች ቁጥጥር ስር ነበር። የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት ከሁለቱም ታጣቂዎች ጋር በመመካከር ከተማዋን መልሶ መቆጣጠር ችሏል። በዋግ ኸምራ ዞን ፃግብጂ ወረዳ አሁንም በትህነግ/ህወሓት ኃይሎች ቁጥጥር ስር ነው። ወረዳውን ከሐምሌ 2013 ጀምሮ ተቆጣጥረውታል (በቅርብ ጊዜ በትህነግ/ህወሓት ኃይሎች እና በአካባቢው የቀበሌ ታጣቂዎች መካከል በፃግብጂ ወረዳ ስለተከሰተው ውጊያ ተጨማሪ መረጃ ለማግኘት ኢፒኦ ሳምንታዊ: ከጥር 27–የካቲት 3, 2015 ይመልከቱ)።7

በተጨማሪም መጋቢት 21 ቀን የፍትህ ሚኒስቴር በትህነግ/ህወሓት ሲቪልና ወታደራዊ አመራሮች ላይ የቀረበውን ክስ አንስቷል።8 በዚህ ምክንያት 36 የትህነግ/ህወሓት አባላት በአዲስ አበባ ከእስር ተፈተዋል።9 የፍትህ ሚኒስቴር እንደገለጸው ክሱ የተሰረዘበት ምክንያት ይህንን ጉዳይ በኢትዮጵያ መንግስት እና በትህነግ/ህወሓት መካከል በጥቅምት 2015 በደቡብ አፍሪካ ፕሪቶሪያ በተፈረመው የሰላም ስምምነት መሰረት “በሽግግር ፍትሕ ማዕቀፍ ውስጥ” ለመመልከት በተደረሰው ስምምነት መሠረት ነው።10 እንዳንድ መረጃዎች ከዚህ ሳምንት ጀምሮ የፌዴራል መንግስት ለትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር የበጀት ድጋፍ ለመልቀቅ መስማማቱን ያመለክታሉ።11 በጀቱ በዚህ ሳምንት መለቀቁ ግን እስካሁን አልተረጋገጠም። የሰላም ሂደቱ እየተካሄደ ባለበት ወቅት የኤርትራ ኃይሎች አሁንም የሰላም ስምምነቱን በመጣስ በትግራይ ክልል አንዳንድ ቦታዎችን እየያዙ ነው የሚል ስጋት አለ።12

በመጨረሻም መጋቢት 16 ቀን ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ የጉራጌ ዞን  እንደ ክልል እንዲቋቋም ባቀረቡት ጥያቄ ላይ ከአካባቢው ነዋሪዎች ጋር ለመምከር በደቡብ ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ክልል የጉራጌ ዞን አስተዳደር ማዕከል ወልቂጤ ከተማ ተጉዘዋል።13  የጉራጌ ዞን ነዋሪዎች ለዓመታት ዞኑ ክልል እንዲሆን ጥያቄ ሲያቀርቡ ቆይተዋል። ይሁን እንጂ መንግሥት ለአንድ የተወሰነ ብሔር ክልል ከመመሥረት ይልቅ በርካታ ዞኖችን ያቀፉ በርካታ ‘ክላስተር ክልሎች’ በደቡብ ክልል እንዲቋቋም ሐሳብ አቅርቧል (ለበለጠ ዝርዝር ኢፒኦ ወርሀዊ: ሰኔ 24 እስከ ሐምሌ 24, 2014 ይመልከቱ)። በጠቅላይ ሚኒስትሩ ጉብኝት ወቅት የወልቂጤ ከተማ ነዋሪዎች ከጠቅላይ ሚኒስትሩ ጋር ለመመካከር የተመረጡት ሰዎች “ስለ ዞኑና ስለ ከተማው በቂ እውቀት የላቸውም” በማለት ከቤት ባለመውጣት ተቃውሞ አሰምተዋል።14 ባለፉት ጥቂት ወራት ውስጥ ነዋሪዎቹ ከራስ አስተዳደር ጥያቄ ጋር በተያያዘ ቢያንስ አምስት ‘በቤት የመቀመጥ/ከቤት ያለመውጣት’ ተቃውሞዎችን አድርገዋል።15 የዞንና የክልል ምክር ቤት አባላትን ጨምሮ ህዝባዊ ተቃውሞውን አስተባብረዋል የተባሉ ቁጥራቸው በውል ያልታወቁ ሰዎች ታስረዋል።16 ከህዳር 15, 2015 ጀምሮ አካባቢው በፌዴራል ፖሊስ እና በደቡብ ክልል ልዩ ኃይል የሚመራ ኮማንድ ፖስት ስር እየተስተዳደረ ይገኛል (ለበለጠ መረጃ ኢፒኦ ሳምንታዊ: ከህዳር 10-16, 2015 ይመልከቱ)።

Footnotes

  1. 2

    ኢዮብ ትኩዬ፣ ‘በደራ ወረዳ ከ100 በላይ ሰዎች በኦነግ ሸኔ ታጣቂዎች መታገታቸው ተገለጸ፣’ ሪፖርተር፣ መጋቢት 20, 2015

  2. 3

    ኢዮብ ትኩዬ፣ ‘በደራ ወረዳ ከ100 በላይ ሰዎች በኦነግ ሸኔ ታጣቂዎች መታገታቸው ተገለጸ፣’ ሪፖርተር፣ መጋቢት 20, 2015

  3. 4

    የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን፣ ‘በከረዩ የሚችሌ ገዳ የጅላ አባላት ግድያ ላይ የተደረገ የምርመራ ሪፖርት፣’ ጥር 25, 2015

  4. 5

    ቦርከና፣ ‘አባ ቶርቤ – የኦሮሞ ድብቅ ነፍሰ ገዳይ ቡድን – አባላት በቁጥጥር ስር መዋላቸውን መንግስት አስታወቀ፣’ ታህሳስ 15, 2011

  5. 6

    የኢትዮጵያ ሚድያ ሰርቪስ፣ ‘ኢኤምኤስ ዜና አዲስ ሐሙስ መጋቢት 21, 2015

  6. 7

    አበበ ፍቅር፣ ‘በአማራ ክልል በዋግ ሕምራ ብሔረሰብ ልዩ ዞን ከ67 ሺሕ በላይ ዜጎች  ለከፋ ረሃብ መጋለጣቸው ተሰማ፣’ ሪፖርተር፣ ታህሳስ 16፣ 2015

  7. 8

    የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዲሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ ፍትህ ሚኒስቴር፣ ‘የክስ መነሳትን አስመልክቶ የተሰጠ መግለጫ፣’ መጋቢት 21, 2015

  8. 9

    ገ/ሚካኤል ገ/መድህን፣ ‘36 የህወሓት አመራሮች ከእስር ተፈቱ፣’ ቮይስ ኦፍ አሜሪካ፣ መጋቢት 21, 2015

  9. 10

    የኢ.ፌ.ዲ.ሪ. ፍትሕ ሚኒስትር፣ ‘የክስ መነሳትን አስመልክቶ የተሰጠ መግለጫ፣’ መጋቢት 21, 2015

  10. 11

    አማኑኤል ይልቃል፤ ‘የፌደራል መንግስት፤ ለትግራይ ክልል የበጀት ድጎማ ለመልቀቅ መስማማቱን አቶ ጌታቸው ረዳ ተናገሩ፤’ መጋቢት 20, 2015

  11. 12

    ሚሊዮን ኃይለስላሴ፣ ነጋሽ መሐመድ፣ ዮሐንስ ገብረእግዚአብሔር፣ ‘ኢሮብ አሁንም በኤርትራ ጦር ቁጥጥር ስር ነዉ-ነዋሪዎች፣’ መጋቢት 22, 2015

  12. 13

    የጠቅላይ ሚኒስትር ቢሮ-ኢትዮጵያ፣ ‘መጋቢት 16, 2015

  13. 14

    ዮናታን ዘብዴዎስ፣ ‘ወልቂጤ ውስጥ ከቤት ያለመውጣት አድማ መደረጉን ነዋሪዎች ተናገሩ።’ ቮይስ ኦፍ አሜሪካ አማርኛ፣ መጋቢት 16, 2015

  14. 15

    ዮናታን ዘብዴዎስ፣ ‘ወልቂጤ ውስጥ ከቤት ያለመውጣት አድማ መደረጉን ነዋሪዎች ተናገሩ።’ ቮይስ ኦፍ አሜሪካ አማርኛ፣ መጋቢት 16, 2015

  15. 16

    ኬኔዲ አባተ፣ ‘በጉራጌ ዞን ከአድማ ጋር በተያያዘ ወጣቶች መታሰራቸው ተነገረ፣’ ቮይስ ኦፍ አሜሪካ አማርኛ፣ ህዳር 14, 2015

Country
Ethiopia
Region
Africa
Share on

Related content