Skip to main content

ኢፒኦ ሳምንታዊ ነሐሴ 27-ጳጉሜ 3, 2015

ይህ ሣዕል በአማራ ክልል የተከሰቱ ጦርነቶች እና ውግእዎችን ይይዛል።

14 September 2023

Also available in English

በቁጥር: ኢትዮጵያ, ነሐሴ 27, 2014-ጳጉሜ 3, 2015

  • የፖለቲካ ግጭት ኩነቶች ብዛት: 1,136
  • በፖለቲካ ግጭቶች ምክንያት ሪፖርት የተደረጉ የሟቾች ቁጥር: 4,034
  • በሰላማዊ ሰዎች ላይ በተሰነዘሩ ጥቃቶች ምክንያት ሪፖርት የተደረጉ የሟቾች ቁጥር: 1,797

በቁጥር: ኢትዮጵያ, ከነሐሴ 27-ጳጉሜ 3, 20151

  • የፖለቲካ ግጭት ኩነቶች ብዛት: 28
  • በፖለቲካ ግጭቶች ምክንያት ሪፖርት የተደረጉ የሟቾች ቁጥር: 85
  • በሰላማዊ ሰዎች ላይ በተሰነዘሩ ጥቃቶች ምክንያት ሪፖርት የተደረጉ የሟቾች ቁጥር: 19

ኢትዮጵያን በተመለከተ በቁጥር የተደገፉ መረጃዎችን ከኢፒኦ የመረጃ መዝገብ እንዲሁም በዋናው የአክሌድ ኤክስፖርት መሳሪያ ውስጥ ማግኘት ይችላሉ።

የሁኔታዎች አጭር መግለጫ

በአማራ ክልል በኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት እና በፋኖ ታጣቂዎች መካከል የሚደረገው ውጊያ ቀጥሏል። ባለፈው ሳምንት አክሌድ በእነዚህ ወገኖች መካከል የተደረገ 18 የጦርነት ኩነቶች እና በኢትዮጵያ አየር ኃይል የተፈፀሙ አራት የሰው አልባ አውሮፕላን ጥቃቶች መዝግቧል። አብዛኛው ውጊያ የተከሰተው በምስራቅ ጎጃም ዞን ቢቡኝ ወረዳ እና በምዕራብ ጎጃም ዞን ደጋ ዳሞት ወረዳ ነው። የሰው አልባ አውሮፕላን ጥቃቶች በደጋ ዳሞት ወረዳ በአረፋ መድኃኒ ዓለም፣ በቢቡኝ ወረዳ ወይን ውሃ እና ሞሴባ ሽሜ አቦ (አዳራሽ) ቀበሌዎች እንዲሁም በሰሜን ሸዋ ዞን አንጾኪያ ወረዳ ማጀቴ ከተማ ተመዝግበዋል (ከዚህ በታች ያለውን ካርታ ይመልከቱ)። በእነዚህ ጥቃቶች ምክንያት ከ50 በላይ ሰዎች መሞታቸው ተነግሯል።

 

ባለፉት አምስት ወራት ውስጥ የአማራ ክልል በኢትዮጵያ እጅግ መረጋጋት ከጎደላቸው ክልሎች አንዱ ሆኗል። በፌዴራል መንግስት እና በፋኖ ታጣቂዎች መካከል ለተፈጠረው ግጭት በርካታ ምክንያቶች አሉ – ብዙ የአማራ ተወላጆች በቅርቡ የተላለፈውን የክልል ልዩ ኃይሎችን ወደ ሌሎች የፀጥታ መዋቅር ለማዋሃድ የተላለፈውን ውሳኔ ለደህንነታቸው አስጊ አድርገው ይመለከቱታል። በሁሉም የሀገሪቱ ክልሎች የሚገኙ የእያንዳንዱ የክልሉ ልዩ ኃይል እንዳደረገው የአማራ ክልል ልዩ ኃይል ለአማራ ህዝብ እና ለአማራ ክልል ከለላ በመሆን አገልግሏል። የፋኖ ታጣቂዎች የሚያደርጉት ትግል ለአማራን ህዝብ ጥቅም ነው ሲሉ መንግስት ግን የፋኖ ታጣቂዎችን በዘረፋ እና የክልሉን ሰላም በማደፍረስ ይከሳቸዋል። ምንም እንኳን በአማራ ክልል የፌዴራል መንግስት የክልል ልዩ ኃይሎችን ወደ ተለያዩ የፀጥታ መዋቅር ለማዋሃድ ማቀዱን ከገለጸ ከሚያዝያ ወር ጀምሮ ውጥረቱ እየጨመረ የመጣ ቢሆንም ከሐምሌ ወር መጨረሻ ጀምሮ በፋኖ ታጣቂዎች እና በኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት መካከል ከፍተኛ የሆነ ውጊያ ተቀስቅሷል። ይህ በቅርብ በክልሉ የተቀሰቀሰውን የፖለቲካ ግጭት የአካባቢው አስተዳደርና የፀጥታ ኃላፊዎች መቆጣጠር አልቻሉም። በመሆኑም የፌዴራል መንግስት ሐምሌ 28 ቀን በአማራ ክልል የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ አውጇል (በአማራ ክልል ስላለው ወቅታዊ ሁኔታ የበለጠ መረጃ ለማግኘት የኢፒኦ ወርሃዊ፡ ከሐምሌ 25 እስከ ነሐሴ 25, 2015ን፤ የኢፒኦ ወርሃዊ፡ ከሰኔ 24 እስከ ሐምሌ 24, 2015ን እና የኢፒኦ ሳምንታዊ: ሐምሌ 22-28, 2015ን ይመልከቱ)

በነሐሴ ወር መጨረሻ የክልሉ መንግስት በአዲስ መልክ እንዲደራጅ የተደረገ ሲሆን የክልሉ ምክር ቤት አዲስ የክልል ርዕሰ መስተዳድርን እና የክልሉን ምክትል አስተዳዳሪን ጨምሮ 12 ባለስልጣናትን በመሾም አዲስ የክልል ካቢኔ አቋቁሟል።2 ይህ የተደረገው የክልሉን የአስተዳደር አቅም ለማሻሻል ነው። አዲሱ የክልሉ ፕሬዝዳንት ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ በመጋቢት 2010 ዓ.ም ወደ ስልጣን ከመጡ በኃላ የተሾሙ አምስተኛው የክልሉ ፕሬዝዳንት ናቸው። በሚያዚያ ወር የአማራ ብልፅግና ፓርቲ ኃላፊ መገደላቸውን ተከትሎ በክልሉ 13 የሚገመቱ የፖለቲካ እና የፀጥታ ባለስልጣናት በታጣቂዎች ጥቃት ደርሶባቸዋል (ለበለጠ መረጃ የኢፒኦ ወርሃዊ፡ ከሰኔ 24 እስከ ሐምሌ 24, 2015ን ይመልከቱ)። ይህም በርካታ የአካባቢና የፀጥታ ኃላፊዎች ቤታቸውን እና መንደራቸውን ለቀው እንዲወጡ በማድረግ በአማራ ክልል የተለያዩ አካባቢዎች የአስተዳደርና የፀጥታ ክፍተት እንዲፈጠር አድርጓል።3 አዲሱ የክልሉ ፕሬዝዳንት አቶ አረጋ ከበደ ስልጣናቸውን ከተረከቡ በኋላ ኃላፊዎችን መሾማቸውን ቀጥለዋል። ባለፈው ሳምንት ጳጉሜ 3 ቀን የተወሰኑ የዞን አስተዳዳሪዎችን እና ምክትል አስተዳዳሪዎችን ጨምሮ 26 የስራ ኃላፊዎችን ሾመዋል።4 በኢትዮጵያ ያሉ ሁሉም ክልሎች የክልል ምክር ቤት እና የዞን፣ የወረዳና የቀበሌ አስተዳደር አላቸው። ከዞን በስተቀር እያንዳንዱ የአስተዳደር እርከን ከምክር ቤት (ህግ አውጭ) በተጨማሪ አስፈጻሚና የፍትህ አካላትን ያቀፉ ናቸው። የክልል፣ የወረዳና የቀበሌ ምክር ቤት አባላት የሚመረጡት በአካባቢው ህዝብ ነው። በዞን ደረጃ እንደዚህ አይነት አደረጃጀት ስለሌለ የክልሉ ፕሬዝዳንት የክልሉ ምክር ቤት ካፀደቀ በኃላ የዞን አስተዳዳሪዎች እና ኃላፊዎችን የሚሾሙ ሲሆን በወረዳ እና በቀበሌ ደረጃ በተለያዩ የሥራ ኃላፊነቶች ላይ ያሉ ኃላፊዎች በወረዳ/ቀበሌ ምክር ቤት ከፀደቁ በኋላ በወረዳ/ቀበሌ አስተዳዳሪ ይሾማሉ።

ካለፉት ሳምንታት ጋር ሲነጻጸር የኦሮሚያ ክልል በአንጻራዊ የመረጋጋት ጊዜ ላይ ይገኛል። ነሐሴ 27 ቀን የኦሮሞ ነፃነት ግንባር (ኦነግ)-ሸኔ በሰሜን ሸዋ ዞን ደራ ወረዳ ጉንዶ መስቀል ወደሚገኝ ገበያ ሲጓዙ የነበሩ ቁጥራቸው በውል የማይታወቁ ሰላማዊ ሰዎችን አፍኖ ወሰዷል። የሪፐብሊካን ጋርድ አባላት በሆሮ ጉዱሩ ወለጋ እና በምስራቅ ወለጋ ዞኖች በኦነግ-ሸኔ ላይ በወሰዱት እርምጃ ቁጥራቸው በውል ያልታወቁ የኦነግ-ሸኔ አባላት ከነጦር መሣሪያዎቻቸው መያዛቸውን የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት ገልጿል። የሪፐብሊካን ጋርድ  የተቋቋመው ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ ወደ ስልጣን ከመጡ በኋላ ነው። ዋና ተግባራቱ ሕገ-መንግሥታዊ ሥርዓቱን ማስጠበቅ እና ከፍተኛ ባለሥልጣናትን እና ቤተሰቦቻቸውን መጠበቅ ነው።5 ሆኖም ቡድኑ በሀገሪቱ ውስጥ በተለያዩ የጦርነት ኩነቶች ላይም ተሳትፎ አድርጓል።

ጳጉሜ 2 ቀን በትግራይ ክልል ሮማናት አደባባይ የትግራይ ጊዜያዊ ክልላዊ መንግስትን በመቃወም ሰላማዊ ሰልፍ ለማድረግ የተሰባሰቡትን የክልሉ ፖሊስ የደበደበ ሲሆን 50 የተቃዋሚ ፓርቲ አባላትና አመራሮችን ጨምሮ ቢያንስ 150 ሰዎችን አስሯል።6 ሰልፉን ያዘጋጁት ሦስት ተቃዋሚ ፓርቲዎች – ሳልሳይ ወያነ ትግራይ፣ የታላቋ ትግራይ ብሔራዊ  ሸንጎ (ባይቶና) እና የትግራይ ነፃነት ፓርቲ – “ህብረት ለስር ነቀል ለውጥ” በሚል መሪ ቃል ነው።7 ሦስቱ ፓርቲዎች በመቀሌ ከተማ ከጳጉሜ 2 ቀን ጀምሮ ለሶስት ቀናት የሚቆይ ሰላማዊ ሰልፍ ጠርተው ነበር።8 ነገር ግን የኢትዮጵያ አዲስ አመት በዓልን ምክንያት በማድረግ በቂ የፀጥታ ኃይሎች ባለመኖራቸው እና በክልሉ ያለውን የፀጥታ ስጋት በመግለፅ ሰልፉን ማካሄድ እንደማይችሉ ጊዚያዊ መንግስቱ ለአዘጋጆቹ አሳውቆ ነበር።9 የፀጥታ ኃይሎች የተቃዋሚ ፓርቲ ደጋፊዎችን እና አመራሮችን ማሰር የጀመሩት ከሰልፉ ቀን ቀደም ብሎ እንደነበር ተዘግቧል።10

የ”ህብረት ለስር ነቀል ለውጥ” ንቅናቄ የትግራይ ህዝብ ነፃነት ግንባር የሚመራው ጊዜያዊ ክልላዊ መንግስት በክልሉ የሚታየውን የፀጥታ ችግር ለመፍታት ብቃት የለውም ብሎ ይከሳል። የሰላማዊ ሰልፉ አዘጋጆቹ በክልሉ ውስጥ ያሉ ሰዎች ዝርፊያን ወይም ግድያን በመፍራት የዕለት ተዕለት ተግባራቸውን ማከናወን ተስኗቸዋል ይላሉ።11 በቅርቡ በሐኪሞች ለሰብአዊ መብቶች እና በአፍሪካ ቀንድ የፍትህ እና ተጠያቂነት ድርጅት በተደረገ ጥናት በጥቅምት 2015 “የሰላም ስምምነቱ ከተፈረመ በኋላ ቢያንስ 128 ጾታዊ ጥቃቶች የተፈጸሙ” ሲሆን  እነዚህን ጥቅቶች “በአብዛኛው ተዋጊ በሆኑ ብዙ ወንዶች” ተፈጽመዋል ብሏል።12 ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በርካታ ሪፖርቶች በክልሉ ያለውን ዝርፊያ እና አስገድዶ መድፈርን ጨምሮ ሰፊ ወንጀል እና ህገ-ወጥነት ዘግበዋል።13 የጊዜያዊ የክልሉ መንግስት ርዕሰ መስተዳድር አቶ ጌታቸው ረዳ የፀጥታ እጦት በክልሉ መኖሩን እና መንግሥታቸው አገልግሎትና ጥበቃን ወደ ገጠር አካባቢዎች ማስፋት አለመቻሉን አምነዋል። ለዚህም በጊዜያዊ የክልሉ መንግስት ውስጥ የሚገኝ ማንነቱ ያልተገለፀ የተደራጀ ቡድንን ተጠያቂ ያደረጉ ሲሆን ይህ ቡድን ከጊዜያዊው መንግስት አስተዳደር በተቃራኒ  እየሰራ ነው በማለት የክልሉ መንግስት እንቅስቃሴ እና በክልሉ ውስጥ ያለውን ተቀባይነት ላይ ተጽእኖ እያሳደረ መሆኑን ገልፀዋል።14

ቀደም ሲል የደቡብ ብሄሮች፣ ብሄረሰቦች እና ህዝቦች ክልል ተብሎ በሚጠራው በቅርቡ በተቋቋመው የመካከለኛው ኢትዮጵያ ክልል በቅበት ከተማ ነሐሴ 29 ቀን ሙስሊም ወጣቶች የቁርዓን ንባባቸውን ለመከልከል በሞከሩ የአካባቢው የፀጥታ ኃይሎች ላይ ድንጋይ ወርውረዋል። የቁርዓን ንባቡ አንዳንድ ሴቶች እንዲታመሙ ምክንያት ሆኗል ብለው የሚያምኑትን መጥፎ መናፍስት ወይም ድግምት ለማስወገድ በማሰብ ነበር። የአካባቢው ፖሊስ ተኩስ ከፍቶ አንድ ወጣት ሲገድል ሌሎች አራት አቁስሏል። ወጣቶቹ እስከ ነሐሴ 30 ቀን አካባቢውን ከአዲስ አበባ ጋር የሚያገናኘውን ዋና መንገድ ዘግተዋል። የአካባቢው የፀጥታ ኃይሎች ጋር ከተጋጩ በኋላ የሙስሊም ወጣቶች ከነሐሴ 29 እስከ 30 ባለው ጊዜ ውስጥ የኦርቶዶክስ ክርስቲያኖች ንብረት የሆኑ ቢያንስ 13 የመኖሪያ ቤቶችን እና “በርካታ” የንግድ ድርጅቶችን እንዲሁም በከተማው ውስጥ የሚገኝ የኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያንን አቃጥለዋል።15 የኦርቶዶክስ ክርስትና ኃይማኖት ተከታዮችን ሴቶችን እያሳመመ ነው ብለው ያመኑትን ድግምት አስርተዋል ሲሉ ከሰዋል። በመቶዎች የሚቆጠሩ የኦርቶዶክስ እምነት ተከታዮች ቤታቸውን ለቀው ለመሰደድ ተገደዋል።

Footnotes

  1. 1

    በዚህ የጊዜ ገደብ ውስጥ የተከሰቱ አንድ አንድ ኩነቶች በዘገባ መዘግየት ምክንያት በቀጣይ ሳምንታት ውስጥ በመረጃ ቋታችን ውስጥ ሊካተቱ ይችላሉ።

  2. 2

    ሲሳይ ሳህሉ፣ ‘በአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ውስጥ የሚገኘው የአማራ ክልል ፕሬዚዳንት ከሥልጣናቸው ተሻሩ፣’ ሪፖርተር፣ ነሐሴ 21, 2015

  3. 3

    የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን፣ ‘በአማራ ክልል የተነሳው ግጭት በሰላማዊ ሰዎች ላይ የፈጠረው የሰብአዊ መብት ተፅእኖ፣’ ነሐሴ 8, 2015

  4. 4

    አማራ ሚዲያ ኮርፖሬሽን፣ ‘ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ ልዩ ልዩ ሹመቶችን ሰጡ፣’ ጳጉሜ 03, 2015

  5. 5

    ዳንኤል ሚምበሬ፣ ‘ፎቶዎች፡ ‘የሪፐብሊካን ጋርድ’ ኢትዮጵያን ለመጠበቅ ያለውን ዝግጁነት አሳይቷል ጠቅላይ ሚኒስትር፣’ አፍሪካኒውስ፣ ታህሳስ 14, 2011

  6. 6

    ሚሊዮን ኃይለሥላሴ፣ ነጋሽ መሐመድ እና ኂሩት መለሰ፣ ‘ፖሊስ በኃይል የበተነው የመቀሌው ሰላማዊ ሰልፍ፣’ ዲደብሊው አማርኛ፣ ጳጉሜ 2, 2015

  7. 7

    ዲደብሊው አማርኛ፣ ‘የነሐሴ 30 ቀን፣ 2015 ዓ.ም የዓለም ዜና፣’ ነሐሴ 30, 2015

  8. 8

    ቦርከና፣ ‘ተቃዋሚዎች በመቀሌ ከተማ አዲስ የፖለቲካ ሥርዓት ለመጠየቅ ወደ ጎዳና ሊወጡ ነው፣’ ነሐሴ 30, 2015

  9. 9

    ቲክቫህ-ኢትዮጵያ፣ ‘በወርሃ ጳጉሜን የተጠየቀው የተቋውሞ ሰላማዊ ሰልፍ ጥያቄ ማስተናገድ እንደማይችል የመቐለ ከተማ አስተዳደር አስታወቀ፣’ ነሔሴ 26, 2015

  10. 10

    ሚሊዮን ኃይለሥላሴ፣ ታምራት ዲንሳ እና ኂሩት መለሰ፣ ‘በመቀሌ በሰላማዊ ሰልፍ ቅስቀሳ ላይ የነበሩ የተቃዋሚ ፓርቲ አባላት ታሰሩ፣’ ዲደብሊው አማርኛ፣ ነሐሴ 30, 2015

  11. 11

    ሚሊዮን ኃይለሥላሴ፣ ኂሩት መለሰ፣ አዜብ ታደሰ፣ ‘«የትግራይ ነፃነት ፓርቲ» በህወሓት ላይ ያቀረበው ክስ፣’ ነሐሴ 11፣ 2015

  12. 12

    ካራ አና፣ ‘አንድ ጥናት በኢትዮጵያ ትግራይ ሰላም ስምምነት ከተደረሰ በኋላ በርካታ ሴቶች እና ልጃገረዶች የፆታ ጥቃት ደርሶባቸዋል አለ፣’ አሶሼትድ ፕሬስ፣ ነሐሴ 18, 2015

  13. 13

    ቪኦኤ አማርኛ፣ ‘በትግራይ ክልል ተባብሷል በተባለው የጸጥታ ችግር የሴቶች ግድያ መበራከቱ ተገለጸ፣’ ነሐሴ 24, 2015

  14. 14

    ትግራይ ቲቪ፣ የጊዜያዊ የትግራይ መንግስት ርዕሰ መስተዳድር አቶ ጌታቸው ረዳ የተሰጠ ጋዜጣዊ መግለጫ፣’ ጳጉሜ 1, 2015

  15. 15

    አዲስ ማለዳ፣ ‘በስልጤ ዞን 13 መኖሪያ ቤቶች እና በርካታ የንግድ ሱቆች መቃጠላቸው ተነገረ፣’ ጳጉሜ 1, 2015

Country
Ethiopia
Region
Africa
Share on

Related content