Skip to main content

ኢፒኦ ሳምንታዊ፡ ጥቅምት 3-9, 2016

Analysis of political conflicts and events in Ethiopia from October 3-9, 2016, focusing on regional armed clashes and statistics.

26 October 2023

Also available in English

በቁጥር፡ ኢትዮጵያ, ጥቅምት 3-9, 20161

  • የፖለቲካ ግጭት ኩነቶች ብዛት፡ 35
  • በፖለቲካ ግጭቶች ምክንያት ሪፖርት የተደረጉ የሟቾች ቁጥር፡ 187
  • በሰላማዊ ሰዎች ላይ በተሰነዘሩ ጥቃቶች ምክንያት ሪፖርት የተደረጉ የሟቾች ቁጥር፡ 24

በቁጥር፡ ኢትዮጵያ, ጥቅምት 4, 2015-ጥቅምት 9, 2016 

  • የፖለቲካ ግጭት ኩነቶች ብዛት፡ 1,178
  • በፖለቲካ ግጭቶች ምክንያት ሪፖርት የተደረጉ የሟቾች ቁጥር፡ 3,813
  • በሰላማዊ ሰዎች ላይ በተሰነዘሩ ጥቃቶች ምክንያት ሪፖርት የተደረጉ የሟቾች ቁጥር፡ 1,514

ኢትዮጵያን የሚመለከቱ በቁጥር የተደገፉ መረጃዎችን ከኢፒኦ የመረጃ መዝገብ እንዲሁም በዋናው የአክሌድ ኤክስፖርት መሳሪያ ውስጥ ማግኘት ይችላሉ፡፡

የሁኔታዎች አጭር መግለጫ

በአማራ ክልል በፋኖ ታጣቂዎች እና በኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት መካከል የሚደረጉ ውጊያዎች እንደቀጠሉ ሲሆን በኦሮሚያ ክልል እገታ እና ውጊያዎች ተዘግበዋል። በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልልም ብሔርን መሠረት ያደረጉ ግጭቶች ተዘግበዋል።

በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ወልቂጤ ከተማ በቀቤና እና በጉራጌ ብሔር ቡድኖች መካከል ጥቅምት 2 ቀን የጀመረው ግጭት ባለፈው ሳምንት እስከ ጥቅምት 4 ቀን ቀጥሏል። ግጭቱ በቀቤና ልዩ ወረዳ እና በወልቂጤ ከተማ መካከል ካለው የወሰን ውዝግብ ጋር የተያያዘ ነው። በግጭቱ ምክንያት ቢያንስ ስድስት ሰዎች ተገድለዋል፡፡ ጥቅምት 4 ቀን ፖሊስ እየተጋጩ የነበሩ ነዋሪዎችን ለመበተን አስለቃሽ ጭስ ተጠቅሟል። በተጨማሪም የጉራጌ ዞን ኮማንድ ፖስት ግጭቱን ለመቆጣጠር የሰዓት እላፊ አውጇል።2 በቅርቡ የተመሠረተው የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የቀቤና እና የማረቆ ወረዳዎችን በ’ልዩ’ ወረዳነት በመመደብ የምስራቅ ጉራጌ ወረዳን ደግሞ ወደ ዞን በማሳደግ ከዚህ ቀደም ሲያቀርቡት በነበረው ጥየቄ መሠረት ከጉራጌ ዞን መዋቅር ስር በመውጣት የራሳቸውን የአስተዳደር መዋቅር በመመስረት ራሳቸውን እንዲያስተዳድሩ ልዩ መብት ሰቷቸዋል።3 እነዚህ አዳዲስ የአስተዳዳር መዋቅሮች ይፋ ከተደረጉ ጊዜ ጀምሮ በክልሉ አልፎ አልፎ ከወሰን ጋር የተያያዙ ግጭቶች እየተከሰቱ መሆኑ ተመዝግቧል (ለተጨማሪ መረጃ የኢፒኦ ሳምንታዊ፡ 19-25 መስከረም 2016ን ይመልከቱ)።

ፋኖ ታጣቂዎችኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት ጋር በአማራ ክልል በምዕራብ ጎጃም ዞን በቡሬ፣ በምስራቅ ጎጃም ዞን በደብረ ማርቆስ፣ በሰሜን ሸዋ ዞን በመተህ ብላ እንዲሁም በሰሜን ወሎ ዞን ቆቦ ከተማ አካባቢ በዞብል ተራራዎች ተዋግተዋል። የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት በክልሉ በሚገኙ ዋና ዋና ከተሞች በመሰማራቱ እና ከፋኖ ታጣቂዎች ጋር ተደጋጋሚ ውጊያዎች ከማድረጉ ጋር በተያያዘ በክልሉ በብዙ አካባቢዎች ከፍተኛ ውጥረት ነግሷል4 (በአማራ ክልል ስላለው ግጭት ተጨማሪ መረጃ ለማግኘት የኢፒኦ ወርሃዊ: ከሐምሌ 25 እስከ ነሐሴ 25, 2015ን ይመልከቱ)። የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት ባለፈው ሳምንት በደሴ ከተማ ”አክራሪ ኃይል” ብሎ የገለፀው ቡድን በተለያዩ የከተማዋ አካባቢዎች ፈንጂዎችን በማጥመድ ሊፈፀሙ የታቀዱ ጥቃቶችን ማክሸፉን የገለፀ ሲሆን በዘገባው መሠረት ጥቃቱ የከተማዋን ፀጥታ እንዲሁም በከተማዋ ሲካሄድ የነበረን የገዢው ፓርቲ ሰልጠናን ለማወክ ያለመ እንደነበር ተገልጿል።5 ገዢው ፓርቲ, ብልጽግና ፓርቲ, የአማራ ክልል ዋና ከተማ ባህርዳር እና ደሴ ከተማን ጨምሮ በሀገር አቀፍ ደረጃ በ10 ተለያዩ ቦታዎች ለ12 ቀናት የዘለቀ ለከፍተኛ እና መካከለኛ አመራሮቹ “ከእዳ ወደ ምንዳ” በሚል መርህ ቃል ስልጠና ሲሰጥ ቆይቷል።6 የአማራ ክልል በክልሉ የተደረጉ ስልጠናዎችን ክልሉ የተረጋጋ መሆኑን ለማሳየት እንደ ምልክት ተጠቅሞበታል።7

ይህ በእንዲህ እንዳለ ባለፈው ሳምንት በኦሮሚያ ክልል በኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት እና በኦሮሞ ነፃነት ግንባር(ኦነግ)-ሸኔ ታጣቂዎች መካከል የተደረጉ 13 ውጊያዎች የተዘገቡ ሲሆን ሁለቱም ኃይሎች በሰላማዊ ሰዎች ላይ በተፈፀሙ ጥቃቶች ላይ ተሳትፈዋል የሚል ወቀሳም ይቀርቦባቸዋል (ከዚህ በታች ያለውን ካርታ ይመልከቱ)። ባለፈው ሳምንት የተዘገቡ አብዛኞቹ ውጊያዎች እና በሰላማዊ ሰዎች ላይ የተፈፀሙ ጥቃቶች በሰሜን ሸዋ ዞን ውስጥ የተከሰቱ ሲሆኑ ይህም በተደጋጋሚ ግጭቶች በሚከሰትበት አማራ ክልልን ከአዲስ አበባ ጋር የሚያገናኘውን አውራ ጎዳና ተከትሎ የተፈፀሙ ናቸው። ውጊያዎች እና በሰላማዊ ሰዎች ላይ የሚፈፀሙ ጥቃቶች በቀጠሉበት ሁኔታ ውስጥ ጥቅምት 9 ቀን በሰሜን ሸዋ ዞን ቢያንስ አራት የቻይና ዜጎች ከሚሰሩበት ሲሚንቶ ፋብሪካ የኦነግ-ሸኔ አባላት መሆናቸው በተገመተ ሰዎች ታግተው ተወስደዋል።8 በግንቦት 2013 ወር በምዕራብ ወለጋ ዞን መንዲ ከተማ አካባቢ ሌሎች ሦስት የቻይና ዜግነት ያላቸው ሠራተኞች በአካባቢው የማዕድን ማውጣት ጋር በተያያዘ ባላቸው ተሳትፎ ምክንያት በኦነግ-ሸኔ ታጣቂዎች ታግተው ተወስደው ነበር። በኃላ ላይ በአለም አቀፉ የቀይ መስቀል አደራዳሪነት ተለቀዋል።9 ባለፈው ሳምንት የተለያዩ ዘገባዎች በኦሮሚያ ክልል በተደጋጋሚ እየተፈፀመ ባለው ሰላማዊ ሰዎችን የማገት ተግባር ምክንያት የክልሉን ነዋሪዎች ስጋት ውስጥ መግባታቸውን አመላክተዋል።10

 

በመጨረሻም በተባበሩት መንግስታት ድርጅት የተቋቋመው በኢትዮጵያ ላይ ትኩረት ያደረገ የሰብአዊ መብቶች ባለሙያዎች ኮሚሽን የመጨረሻ ሪፖርቱን እና ግኝቶቹን ጥቅምት 2 ቀን በ54ኛው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የሰብአዊ መብቶች ጉባኤ ስብሰባ ወቅት አውጥቷል። ሪፖርቱ ሌሎች ጉዳዮችን ጨምሮ “የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት፣ የኤርትራ መከላከያ ሠራዊት፣ የክልል ኃይሎች እና ከእነሱ ጋር ግንኙነት ያላቸው ታጣቂዎች በትግራይ በሰዎች ላይ የመብት ጥሰት እና እንግልት መፈጸማቸውን…እነዚህም ድርጊቶች የጦር ወንጀል እና በሰዎች ላይ የሚፈፀም ወንጀል ናቸው” በማለት ግኝቶቹን አስቀምጧል።11 ኮሚሽኑ የትግራይ ተዋጊዎችም በአማራ እና በአፋር ክልሎች በጦር ወንጀል ስር ሊመደቡ የሚችሉ ድርጊቶችን መፈፀማቸውን ያረጋገጠ ሲሆን የአማራ እና የኤርትራ ኃይሎች ሪፖርቱ በሚዘጋጅበት ወቅትም በትግራይ ክልል ወሰን ውስጥ በመሆናቸው እነዚህ ግጭቶች እና ወንጀሎች አሁንም እየተፈፀሙ መሆናቸው እንደሚያሳስበው ገልጧል። ቀደም ሲል ኮሚሽኑን የደገፉ የአውሮፓ ሕብረት ዲፕሎማቶች በተደረገላቸው ቃለ መጠይቅ የኮሚሽኑ የስልጣን ዘመን በ54ኛው የሰብአዊ መብቶች ጉባኤ ስብሰባ ወቅት የመገባደዱን አስፈላጊነት ገልፀው የኢትዮጵያ መንግስት በተፈፀሙ የሰብአዊ መብቶች ጥሰቶች ላይ የተጀመረውን ምርመራ ያስቀጥላል ብለ እንደሚጠብቁ አስረድተዋል።12 የኢትዮጵያ መንግስት ከጅምሩ የኮሚሽኑን መቋቋም በመቃወም ኮሚሽኑ እንዲቋረጥ ጥሪ ያቀረበ ሲሆን ኮሚሽኑንም የሰብአዊ መብትን ለፖለቲካ ፍጆታ አውሎታል በማለት ከሶ ነበር።13

Footnotes

  1. 1

    በዚህ የጊዜ ገደብ ውስጥ የተከሰቱ አንድ አንድ ኩነቶች በዘገባ መዘግየት ምክንያት በቀጣይ ሳምንታት ውስጥ በመረጃ ቋታችን ውስጥ ሊካተቱ ይችላሉ።

  2. 2

    የጉራጌ ዞን የመንግስት ኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ዲፓርትምንት፣ ‘በጉራጌ ዞን ኮማንድ ፖስት የተሰጠ መግለጫ,’ ጥቅምት 3, 2016

  3. 3

    ዋዜማ ራዲዮ፣ የደቡብ ብሄሮች፣ ብሄረሰቦችና ሕዝቦች ክልል ሕልውና በይፋ አከተመ፣’ ነሐሴ 13, 2015

  4. 4

    ማንተጋፍቶት ስለሺ፣ ‘አማራ ክልል በመከላከያና የፋኖ ፍጥጫ ውጥረት አይሏል’ ዶይቼ ቬለ አማርኛ፣ ጥቅምት 7, 2016

  5. 5

    የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዴሞክራሲያዊ ሪፓብሊክ የመከላከያ ሠራዊት፣ ’በደቡብ ወሎ ዞን ደሴ ከተማ የፅንፈኛ ቡድን ሰርጎ ገቦች የህብረተሰቡን ሠላም ለማወክ ሲዘጋጁ በመከላከያ ሠራዊታችን በቁጥጥር ሥር ዋሉ፣’ ጥቅምት 10, 2016

  6. 6

    ብልጽግና ፓርቲ፣ “የብልጽግና ፓርቲ ከፍተኛ እና መካከለኛ አመራሮች የሚሳተፉበት 2ኛ ዙር የስልጠና መድረክ በዛሬው እለት ተጀምሯል፣’ መስከረም 29, 2016

  7. 7

    አማራ ሚዲያ ኮርፖሬሽን፣ ’’በአማራ ክልል የተካሄደው ሥልጠና የተለየ ትርጉም እና አንድምታ አለው’ ርእሰ መሥተዳድር አረጋ ከበደ፣’ ጥቅምት 10, 2016

  8. 8

    አዲስ ስታንዳርድ፣ ‘ቁጥራቸው በውል ያልታወቀ ቻይናውያን በሰሜን ሸዋ ዞን ውስጥ በታጠቁ ሰዎች ታገቱ፣’ ጥቅምት 9, 2016

  9. 9

    አዲስ ስታንዳርድ፣ ‘የኦሮሞ ነፃነት ሠራዊት እንደያዛቸው ያሳወቀው  ሦስት የቻይና ዜጎች ተለቀው ለአለም አቀፍ የቀይ መስቀል ኮሚቴ ተወካዮች ተሰጥተዋል፣’ ግንቦት 21, 2013

  10. 10

    ቪኦኤ አማርኛ፣ ‘በኦሮሚያ ክልል በዜጎች ላይ የሚፈፀመው እገታ በመባባሱ ነዋሪዎች ከቀያቸው እየለቀቁ መሆኑን ተናገሩ፣’ ጥቅምት 9, 2016

  11. 11

    በኢትዮጵያ ላይ ትኩረት ያደረገ አለም አቀፍ የሰብአዊ መብቶች ባለሙያዎች ኮሚሽን፣ ‘ሁሉን አቀፍ የምርመራ ግኝቶች እና የህግ ውሳኔያችው፣’ ጥቅምት 2, 2016

  12. 12

    አሶሺዬትድ ፕሬስ ዜና፣ ‘በተመድ የሚደገፈው በኢትዮጵያ የተፈፀሙ የመብት ጥሰቶች ምርመራ ሊቆም ነው። ማንም አካል እንዲቀጥል አልጠየቀም፣’ መስከረም 23, 2016

  13. 13

    አሸናፊ እንዳለ፣ ‘የተመድ የሰብአዊ መብቶች ባለሙያዎች ስልጣን እንዲቋረጥ ኢትዮጵያ ጠየቀች፣’ የኢትዮጵያ ሪፖርተር, ታኅሳስ 8, 2015

Related content