Skip to main content

ኢፒኦ ሳምንታዊ፡ ኅዳር 22-28, 2016

Reports of continued airstrikes and attacks in Amhara and Oromia regions in Ethiopia.

5 January 2024

Also available in English

  • የፖለቲካ ግጭት ኩነቶች ብዛት፡ 16
  • በፖለቲካ ግጭቶች ምክንያት ሪፖርት የተደረጉ የሟቾች ቁጥር፡ 32
  • በሰላማዊ ሰዎች ላይ በተሰነዘሩ ጥቃቶች ምክንያት ሪፖርት የተደረጉ የሟቾች ቁጥር፡ 8
  • የፖለቲካ ግጭት ኩነቶች ብዛት፡ 1,256
  • በፖለቲካ ግጭቶች ምክንያት ሪፖርት የተደረጉ የሟቾች ቁጥር፡ 3,373
  • በሰላማዊ ሰዎች ላይ በተሰነዘሩ ጥቃቶች ምክንያት ሪፖርት የተደረጉ የሟቾች ቁጥር፡ 1,276

ኢትዮጵያን የሚመለከቱ በቁጥር የተደገፉ መረጃዎችን ከኢፒኦ የመረጃ መዝገብ  እንዲሁም በዋናው የአክሌድ  ኤክስፖርት መሳሪያ  ውስጥ ማግኘት ይችላሉ።

የሁኔታዎች አጭር መግለጫ

ባለፈው ሳምንት በአማራ ክልል የአየር ጥቃቶች እና ውጊያዎች እንደቀጠሉ ሲሆን በኦሮሚያ ክልል በኦርቶዶክስ ክርስቲያኖች ላይ  የተፈጸሙ ጥቃቶች እና ውጊያዎች ተዘግበዋል። ይህ በእንዲህ እንዳለ የኢትዮጵያ ዋና ከተማ በሆነችው በአዲስ አበባ ጦርነትን ለመቃወም ከተጠራ ሰልፍ ጋር በተያያዘ በመቶዎች የሚቆጠሩ ሰዎች ታስረዋል።

በአማራ ክልል በመንግሥት የሚደረገው የሰው አልባ አውሮፕላን ጥቃት የቀጠለ ሲሆን በሳምንቱ ውስጥ በግምት 20 ሰዎች የተገደሉበት ቢያንስ ሁለት ጥቃቶች ተዘግበዋል። ኅዳር 25 ቀን የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት በሰሜን ሸዋ ዞን ውስጥ በመንዝ እና በመራቤቴ ከተሞች መካከል የተሰበሰቡ የፋኖ ኃይሎችን ኢላማ በማድረግ በፈፀማቸው ብዙ ጥቃቶች ሰላማዊ ሰዎችን ጨምሮ ቢያንስ 10 ሰዎች ተገድለዋል። በደቡብ ወሎ ዞን ወገልጤና ከተማ አካባቢ በተፈፀመ ሁለተኛ የሰው አልባ አውሮፕላን ጥቃት አሁንም ሰላማዊ ሰዎችን ጨምሮ አስር ሰዎች ተገድለዋል። በመንግሥት የመገናኛ ብዙሃን በተለቀቀ የቃለ ምልልስ የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት ኢታማጆር ሹም ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት በሰው አልባ አውሮፕላን እየተደገፈ እንደሆነ አምነው አሁንም የ”ጽንፈኞችን” ስብስቦች ኢላማ ማድረጉን እንደሚቀጥሉበት አረጋግጠዋል።2  በተጨማሪም ባለፈው ሳምንት በባሕርዳር ከተማ እና በሰሜን ወሎ ዞን ቡግና አራዶም እና ሮቢት ከተሞች በኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት እና በፋኖ ታጣቂዎች መካከል ውጊያዎች መደረጋቸው ተዘግበዋል (ከታች ያለውን ካርታ ይመልከቱ)።

በኦሮሚያ ክልል በአርሲ ዞን የኦርቶዶክስ ክርስቲያኖች ላይ የሚፈፀሙ ጥቃቶች ቀጥለዋል። ኅዳር 24 ቀን ማንነታቸው ያልታወቀ ታጣቂዎች በሽርካ ወረዳ ጥዮ ለቡ ቀበሌ በኦርቶዶክስ ክርስቲያኖች ላይ ጥቃት በመፈፀም አምስት ሰዎችን ገድለዋል። ባለፉት ሁለት ሳምንታት በዚሁ አካባቢ በተፈፀሙ ተመሳሳይ ጥቃቶች በደርዘን የሚቆጠሩ ሰዎች ተገድለዋል (ለተጨማሪ መረጃ የኢፒኦ ሳምንታዊ፡ ኅዳር 15-21, 2016ን ይመልከቱ)። ባለፈው ሳምንት በኦሮሞ ነፃነት ሠራዊት (በመንግሥት የኦሮሞ ነፃነት ግንባር (ኦነግ)-ሸኔ ተብሎ የሚጠራ) እና በኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት መካከል በዚሁ አካባቢ ውጊያዎች መደረጋቸውም ተዘግቧል። እንዲሁም በእነዚሁ ቡድኖች መካከል በሰሜን ሸዋ ዞን ተጨማሪ ውጊያዎች መደረጋቸው ተዘግቧል።

በመዲናዋ አዲስ አባበ የፌዴራል ፖሊስን ጨምሮ ከተለያዩ የፀጥታ መዋቅር የተወጣጣ የጋራ ግብረ ኃይል ጦርነትን ለመቃወም ለኅዳር 30 ቀን ታቅዶ ከነበረ ሰልፍ ጋር በተያያዘ “ረብሻ እና አለመረጋጋት” ለመፍጠር አቅደዋል ያላቸውን ከ100 በላይ ሰዎችን በቁጥጥር ስር ማዋሉን አስታውቋል።3 የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋር ምክር ቤት በአዲስ አበባ ባወጣው መግለጫ የተጠራውን የተቃውሞ ሰልፍ “ተገቢ ያልሆነ እና ጊዜውን ያልጠበቀ” በማለት ገልፆታል።4 በቁጥጥር ስር ከዋሉ ሰዎች መካከል የኢትዮጵያ አብዮታዊ ፓርቲ ሊቀመንበር እና የቀድሞ የኢትዮጵያ ዜጎች ለማህበራዊ ፍትህ ፓርቲ (ኢዜማ) አባል ይገኙበታል። የሰላም ሚኒስቴር ሚኒስትር ዴኤታ አቶ ታዬ ደንደኣ መንግሥት ጦርነትን የሚቃወም ሰልፍን መከልከሉን በግልጽ ከወቀሱ በኋላ ታኅሣሥ 1 ቀን ከስልጣናቸው እንዲነሱ ተደረጉ ሲሆን በሚቀጥለው ቀን በቁጥጥር ስር ውለዋል።5 ከመንግሥት ጋር ግንኙነት ያላቸው ሚዲያዎች የቀድሞውን ሚኒስትር ዴኤታ “አለመረጋጋት በመፍጠር እና በመሳሪያ መንግሥትን ከስልጣን ለማንሳት በማቀድ ከፀረ ሠላም ኃይሎች” ጋር ተባብረዋል በሚል ከሷቸዋል።6 የኢትዮጵያ መንግሥት እና በኦሮሞ ነፃነት ሠራዊት/ኦነግ-ሸኔ መካከል የተደረገው የሰላም ንግግር ያለስምምነት ከተጠናቀቀ  በኋላ ንግግሩ እየተካሄደ በነበረበት ወቅት በመንግሥት በኦሮሞ ነፃነት ሠራዊት/ኦነግ-ሸኔ ላይ የተወሰዱ የወታደራዊ ኦፕሬሽኖችን አውግዘው ነበር።7

ከአማራ እና ኦሮሚያ ክልሎች በስተቀር ሌሎች የኢትዮጵያ ክፍሎች ይህ ነው የሚባል የተዘገበ የፖለቲካ ግጭት በሌለበት ሰላማዊ ሆነው ቀጥለዋል። ይህ ሁኔታ በደቡብ ኢትዮጵያ እና በቤንሻንጉል/ጉሙዝ የተፈጠሩ ግጭቶች በሀገሪቷ ከተዘገቡ አጠቃላይ የፖለቲካ ግጭቶች ትልቁን ድርሻ ይዘው ከነበረበት ከቅርብ ዓመታት ጋር ሲነጻጸር ጉልህ ለውጥ ነው (በኢትዮጵያ የግጭት ሂደትን በሚመለከት ተጨማሪ መረጃ ለማግኘት የኢፒኦ ወርሃዊ፡ ነሐሴ 26, 2015 እስከ መስከረም 19, 2016ን ይመልከቱ)።

Share on

Related content