ኢትዮጵያ ሳምንታዊ ዘገባ (ኅዳር 3, 2017)
Update on conflicts and events in Amhara region including air strikes and internal tension.
Also available in English
የሁኔታዎች አጭር መግለጫ
በ2015 በአማራ ክልል ግጭት ከጀመረ ወዲህ በአንድ ጊዜ ብዙ ሰዎች የተገደሉበት የአየር ጥቃትን ጨምሮ ባለፈው ሳምንት በክልሉ የተፈፀሙ የአየር ጥቃቶች እና ውጊያዎች የተገደሉ የሰላማዊ ሰዎች ቁጥር እንዲጨምር ምክንያት ሆነዋል። ይህ በእንዲህ እንዳለ የትግራይ ህዝብ ነፃነት ግንባር (ትህነግ/ህወሓት) ውስጥ ያለው አለመግባባት እየተባበሰ የመጣ ሲሆን የጊዜያዊ አስተዳደሩ በደብረጽዮን የሚመራውን ቡድን መፈንቅለ መንግሥት ሊባሉ የሚችሉ ድርጊቶችን በመፈፀም ከሷል።
በአማራ ክልል በሚፈፀሙ የአየር ጥቃቶች የሚገደሉ ሰላማዊ ሰዎች ቁጥር መጨመር
ባለፈው ሳምንት በአማራ ክልል በኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት በተፈፀሙ የአየር ጥቃቶች እና ከፋኖ ታጣቂዎች ጋር የተደረጉ ውጊያዎችን ተከትሎ ሰላማዊ ሰዎች ላይ ባነጣጠሩ ጥቃቶች ምክንያት የተገደሉ የሰላማዊ ሰዎች ቁጥር ጨምሯል.
ጥቅምት 26 ቀን በምዕራብ ጎጃም ዞን ደቡብ አቸፈር ወረዳ ዝብስቲ (አርጌ) ከተማ የሚገኙ የገበያ ቦታ፣ የአንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት እና የጤና ማዕከል ላይ ተደጋጋሚ የአየር ጥቃት የተፈፀመ ሲሆን በጥቃቱ ቢያንስ 43 ሰዎች መገደላቸው የተዘገበ ሲሆን ይኽውም በአማራ ክልል ግጭት ከተጀመረ ወዲህ በአንድ ጊዜ ብዙ ሰዎች የተገደሉበት የአየር ጥቃት ሆኗል። በጥቃቱ 13 ህፃናት እና ብዙ እርጉዝ ሴቶች እንዲሁም የጤና ባለሙያዎች ከተገደሉ ሰዎች መካከል ይገኙበታል1 በተመሳሳይ ቀን በፋኖ ታጣቂዎች እና በኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት መካከል በደቡብ አቸፈር ወረዳ ዱርቤቴ ከተማ ሲደረግ በነበረው ውጊያ ላይ ሌላ ሁለተኛ የአየር ጥቃት መፈፀሙ ተዘግቧል። በአየር ጥቃቱ 16 የፋኖ ታጣቂዎች እና ሦስት ሰላማዊ ሰዎችን ጨምሮ በአጠቃላይ 19 ሰዎች መገደላቸው ተነግሯል።
በሰሜኑ የኢትዮጵያ ግጭት የመጨረሻ አጋማሽ ላይ መንግሥት የድሮን ቴክኖሎጂን ካገኘ ጊዜ ጀምሮ የአየር ጥቃቶች መንግሥት የፀረ-መንግሥት ታጣቂዎችን ለመዋጋት የሚጠቀምባቸው ዋንኛ ስትራቴጂ ሆነዋል። ከ2013 ጀምሮ በኦሮሚያ፣ አማራ እና ትግራይ ክልሎች የሚፈፀሙ የድሮን ጥቃቶች በተደጋጋሚ ለሰላማዊ ሰዎች ሞት ምክንያት ሲሆን ይኽውም ከአለም አቀፍ ማህበረሰብ ወቀሳን አስከትሏል2 የአማራ ክልል ግጭት ከጀመረ ጊዜ ጀምሮ አክሌድ በግምት 431 ሪፖርት የተደረጉ ሰዎች የተገደሉበትን 50 የአየር ጥቃቶችን መዝግቧል — ራቅ ባሉ የሀገሪቷ አካባቢዎች የሚፈፀሙ የድሮን ጥቃቶችን ለመዘገብ ያለው አስቸጋሪ ሁኔታ ሲታይ ይህ አሃዝ ዝቅተኛ ግምት ሊሆን ይችላል። ብዙ ሰዎች የተገደሉበት የድሮን ጥቃት ባለፈው ሳምንት በዝብስቲ ከመፈፀሙ በፊት ብዙ ሰዎች ከተገደሉበት የድሮን ጥቃት የተመዘገበው በየካቲት 2016 በሰሜን ሸዋ ዞን ሞጃን ወደራ ወረዳ በአንድ የጭነት ተሽከርካሪ ላይ በመንግሥት በተፈፀመ የአየር ጥቃት ሲሆን በዚህም ጥቃት 30 ሰዎች ሲገደሉ ሌሎች 15 ሰዎች ቆስለዋል። በጥቅምት ወር መጨረሻ ላይ የአማራ ብሔርተኛ ድርጅት የሆነው የአማራ ማሕበር በአሜሪካ ከመስከረም 15 እስከ ጥቅምት 14 መካከል ባሉ ቀናት በ22 ወረዳዎች ውስጥ የተፈፀሙ የአየር ጥቃቶች መሆናቸው የተጠረጠሩ 43 ጥቃቶችን ዝርዝር የያዘ ሪፖርት ይፋ አድርጓል3 ይሁንና ሪፖርቱ እስከ አሁን በሌላ ሶስተኛ ወገን አልተረጋገጠም።
በተመሳሳይ ወቅት በፋኖ ታጣቂዎች እና በኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት መካከል የሚደረጉ ውጊያዎች የቀጠሉ ሲሆን በአዊ፣ ማዕከላዊ ጎንደር፣ ምስራቅ ጎጃም፣ ምዕራብ ጎጃም፣ ሰሜን ወሎ እና ደቡብ ወሎ ዞኖች ውጊያዎች ተመዝግበዋል። በጥቅምት መጀመሪያ የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት እና የአማራ ክልል ባለሥልጣናት በፋኖ ላይ የሚደረግን ዘመቻ ለማጠናከር ከዛቱ በኋላ ውጊያዎች የተባባሱ ሲሆን— ከመስከረም 21 እና ጥቅምት 29 መካከል ባለው ጊዜ ውስጥ የተደረጉ ውጊያዎች ከቀደሙት ስድስት ሳምንታት ጋር ሲወዳደሩ በ30% ጨምረዋል። የፋኖ ታጣቂዎች በበኩላቸው የአካባቢ አመራሮችን ኢላማ ማድረጋቸውን ቀጥለዋል። ኅዳር 1 ቀን የፋኖ ታጣቂዎች አባል መሆናቸው የተጠረጠሩ ታጣቂዎች የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎችን ኢላማ በማድረግ በቆቦ ከተማ በሚገኝ አንድ ሆቴል ውስጥ በከፈቱት ተኩስ የከተማዋን የብልጽግና ፓርቲ ጸ/ቤት ኃላፊ የገደሉ ሲሆን የከተማዋን የመሬት ምዝገባ ቢሮ ኃላፊ እና ሌሎች ሁለት ሰላማዊ ሰዎችን አቁስለዋል4
በትህነግ/ህወሓት ውስጥ ያለው ልዩነት እየሰፋ መሄድ
በትህነግ/ህወሓት ቡድኖች መካከል የተፈጠረው የውስጥ ልዩነት — አንደኛው በአሁኑ የትህነግ/ህወሓት ሊቀመንበር በደብረጽዮን ገብረሚካኤል የሚመራ ቡድን ሲሆን ሌላኛው ደግሞ የትግራይ ጊዜያዊ አስተዳደር ፕሬዝዳንት ተደርገው በፌዴራል መንግሥት በተሾሙት በጌታቸው ረዳ የሚመራ ቡድን — እየተባባሰ ቀጥሏል። ኅዳር 1 ቀን የጊዜያዊ አስተዳደሩ የደብረጽዮንን ቡድን “የአካባቢ አስተዳደር እንቅስቃሴዎችን ከማደናቀፍ የመፈንቅለ መንግሥት ሙከራ ወደ ማድረግ” ተሸጋግሯል በማለት ከሶታል5 በተጨማሪም የደብረጽዮን ቡድን የትግራይ ታጣቂ ኃይል አመራሮች የእነሱን ቡድን መደገፋቸውን እና የክልሉን መንግሥት ለመቆጣጠርም መቃረባቸውን የሚገልፁ የውሸት መረጃዎችን እያሰራጨ ነው በሚል ከሶታል6 በማዕከላዊ ዞን አስተዳዳሪ መሠረት አምስት ማንነታቸው ያልተገለፀ የክልሉ ታጣቂዎች፣ ፖሊስ እና የፀጥታ ኃላፊዎች አክሱም የሚገኘው የዞኑ መዝገብ ቤት ቢሮን የክልሉን ጊዜያዊ አስተዳደር ማህተብ እንዳይጠቀም ከልክለዋል። የመዝገብ ቤት ሠራተኛዋ ትዕዛዙን ባለመቀበሏ የፀጥታ ኃይሎቹ ሠራተኛዋን ‘አፍነው’ ወደ አድዋ ከተማ የወሰዱዋት ሲሆን እስከ አሁንም ያለችበት ቦታ የማይታወቅ መሆኑን የማዕከላዊ ዞን አስተዳዳሪው ጨምሮ ገልጿል7
በጥቅምት ወር የደብረጽዮን ቡድን የመቐለ ከተማ አስተዳዳሪን አባላቸው በሆነ ሌላ ሰው ተክቷል። ይህ ውሳኔ በኋላ ላይ በመቐለ ከተማ ምክር ቤት የፀደቀ ሲሆን በዚህም በጊዜያዊ አስተዳደሩ የተሾመው ከንቲባ ከስልጣን እንዲነሳ ተደርጓል። ጌታቸው ይህንን ሹመት በመቃወም የመንግሥት ሠራተኞች በአዲሱ ከንቲባ የተላለፈውን ውሳኔ እና የሚሰጡ ሥራዎችን እንዳይቀበሉ አዘዋል8 ይሁንና የመቐለ ምክር ቤት የጊዜያዊ አስተዳደሩ በምክር ቤቱ ላይ ስልጣን የለውም በማለት እነዚህን ትዕዛዞችን ሳይቀበል ቀርቷል። በምክር ቤቱ መሠረት የፕሪቶሪያው ስምምነት — በትህነግ/ህወሓት እና በኢትዮጵያ መንግሥት መካከል የተፈረመው ስምምነት — የክልል እና የዞን ምክር ቤቶችን እንጂ ከመስከረም 2012 በፊት የተመረጠ የከተማ ምክር ቤትን አላፈረሰም በማለት የተከራከረ ሲሆን ይህም የዋና ከተማዋን ከጊዜያዊ አስተዳደሩ ቁጥጥር ውጪ ያደርጋታል9 (በትህነግ/ህወሓት ውስጥ የተፈጠረውን ልዩነት በሚመለከት ተጨማሪ መረጃ ለማግኘት የኢፒኦ ወርሃዊ ከመስከረም 21 እስከ ጥቅምት 21 ዘገባን ይመልከቱ)።
ይህ በእንዲህ እንዳለ በክልሉ ትንታግ ወለዶ ትግራይ የተባለ ትህነግ/ህወሓትን ከስልጣን ማውረድ ላይ ትኩረት ያደረገ አዲስ ንቅናቄ መመስረቱ ተነግሯል። ይህ ቡድን የትግራይ መከላከያ ኃይል አባላትንም ይጨምሮ የተለያዩ በትግራይ ውስጥ እና ከሀገር ውጪ የሚገኙ ግለሰቦችን ያካትታል። ይህ ቡድን አዲስ የተመረጠ መንግሥት ስልጣን እስኪይዝ ድረስ የጊዜያዊ መንግሥትን ከስልጣን ለማንሳት እንደማይፈልግ ገልጿል። በተጨማሪም በቡድኑ አባላት ላይ ምንም አይነት እርምጃ ከተወሰደ የአፀፋ ምላሽ እንደሚሰጥ የገለፀ ሲሆን ነገር ግን ምላሹ በምን መልኩ እንደሆነ ግልጽ አላደረገውም10

ኢትዮጵያ በጨረፍታ
ጥቅምት 23-29, 2017
ይህ መረጃ/ዳታ ከጥቅምት 9 እስከ 15, 2017 ያለውን ጊዜ ይሸፍናል። አክሌድ መረጃን እንዴት እንደሚሰበስብ እና ኩነቶችን እንዴት እንደሚመድብ ተጨማሪ መረጃ ለማግኘት የአክሌድን የኮድ መጽሐፍን ይመልከቱ። በዚህ የጊዜ ገደብ ውስጥ የተከሰቱ አንዳንድ ኩነቶች በዘገባ መዘግየት ምክንያት በሚቀጥሉት ሳምንታት ዳታ ውስጥ ሊካተቱ ይችላሉ።
Footnotes
- 1
ቢቢሲ አማርኛ፣ ‘በሰሜን ጎጃም በድሮን ጥቃት ነፍሰ ጡር ሴቶችን ጨምሮ 50 የሚሆኑ ሰዎች መገደላቸውን የዓይን እማኞች ተናገሩ፣’ ጥቅምት 28, 2017
- 2
- 3
የአማራ ማሕበር በአሜሪካ፣ ‘በአማራ ክልል በቅርቡ የተመዘገቡ ድሮን እና የአየር ትቃቶች አጠቃላይ ዘገባ፣ ኢትዮጵያ፣’ ጥቅምት 20, 2017
- 4
- 5
ሪፖርተር፣ ‘ቡድኑ “በይፋ መፈንቅለ መንግሥትን ወደ መፈጸም ተሸጋግሯል”፣” የትግራይ ጊዜያዊ አስተዳደር፣’ ኅዳር 1, 2017
- 6
ቢቢሲ አማርኛ፣ ‘በትግራይ መፈንቅለ መንግሥት እና ሥርዓት አልበኝነት የተባሉት ክስተቶች ምንድን ናቸው?፣’ ኅዳር 3, 2017
- 7
ቢቢሲ አማርኛ፣ ‘በትግራይ መፈንቅለ መንግሥት እና ሥርዓት አልበኝነት የተባሉት ክስተቶች ምንድን ናቸው?፣’ ኅዳር 3, 2017
- 8
ሙሉጌታ አጽበሃ፣ ‘በአወዛጋቢው የመቐለ ከንቲባ ጉዳይ በከተማው ምክር ቤት ውይይት ሊደረግ ነው ተባለ፣’ ቪኦኤ አማርኛ ፣ ጥቅምት 20, 2017
- 9
ቢቢሲ አማርኛ፣ ‘በትግራይ መፈንቅለ መንግሥት እና ሥርዓት አልበኝነት የተባሉት ክስተቶች ምንድን ናቸው?፣’ ኅዳር 3, 2017
- 10
- 11
ይህ ውጊያዎችን፣ ፍንዳታዎች/ የርቀት ግጭት እና ሰላማዊ ሰዎች ላይ የሚደርሱ ጥቃቶችን የሚመለከቱ ኩነቶችን እንዲሁም የአመፅ ግጭት ንዑስ ኩነት የሆነውን የአመፅ ኩነትን ይጨምራል።
- 12
ይህ የተቃውሞ ሰልፎች የኩነት አይነትን እንዲሁም የአመፅ ግጭት ንዑስ ኩነት የሆነውን ግጭት ያለበት የተቃውሞ ሰልፍ ኩነትን ይጨምራል።